tgoop.com/Zephilosophy/1109
Last Update:
የፈላስፋ ህይወት በምን ይገለፃል?
የአማርኛው መዝገበ ቃላት “ፈለሰፈ” እንዲሁም “ፍልሰፋ” የሚሉትን ቃላት ልዩ ልዩ ብልሃትንና ጥበብን ከአእምሮ እያመነጨ አስገኘ፣ ያልነበረውን የጥበብ ሥራ ፈጥሮ አገኘ፣ ያልተገለጠውን (ያልታወቀውን) እንዲታወቅ አደረገ፣ ጥበብን(እውቀትን) ወደደ በማለት ትርጉም ሰጧቸዋል፡፡
የሚከተሉት ባህሪዎች ደግሞ ፈላስፋዎች የሚኖሩትን ህይወት ሊያመለክቱ የሚችሉ ዋና ዋና መገለጫዎች ናቸው።
1.ፈላስፋዎች የእውቀት ሱሰኞች ናቸው፤ አዲስን ነገር ለማወቅ የተራቡ ናቸው:: ነጋም መሸም ያው ነው - እውቀትን መፈለግ የጊዜ ገደብ የለውም፡፡ ለፈላስፋ ጊዜ፣ ቦታ፣ ሁኔታ እውቀት ማስገኘት አለባቸው፡፡ ለፈላስፋ እውቀት በልተው የማይጠግቡት የሚጣፍጥ ምግብ ነው፣ ጠጥተው የማይረኩት ጣፋጭ ወይን ጠጅ ነው፡፡ ሰዎች፣ ተፈጥሮ. ሌላም ሌላም... እግዚአብሔርም ይሁን ለፈላስፋ ሁሉም እውቀት ናቸው፡፡ ተፈጥሮ የያዘችው የሚያስደምም ህብርና ሥርዓት ምስጢር ማወቅ ጉጉታቸው መጠን የለውም፡፡ የሰውን ግላዊ፣ ማኅበራዊና ተፈጥሯዊ ማንነቱን፣ ተስፋውንና ጭንቀቱን ለማወቅ ሥሥት ያደረባቸው ናቸው፡፡ ፈላስፋ ለማንም አይገዛም ቢባል የተጋነነ አይሆንም፣ ግለ - ታሪካቸው ይመስክራልና፡፡ ነገር ግን ለማንም የማይረታው ልቦናቸው ለአንድ ነገር ተሸናፊና ባሪያ ነው - ለእውቀት!
2.ፈላስፋዎች ሌላው የሚታወቁበት ነገር ለሰው ልጅ እጅግ አሳቢዎች መሆናቸው ነው:: ከማንም በላይ ህብረተሰብ የሚሠቃይባቸው ችግሮች ይሰማቸዋል፡፡ ህብረተሰብን ለከፋ ህመም የዳረጉ ቁስሎች እነርሱንም ይጠዘጥዛቸዋል፡፡ ህብረተሰብ ገመናውን በይስሙላ ከበሮችና ወዳሴዎች መሸፈኑ ያንገበግባቸዋል፡፡ ለፈላስፋ የሰው ልጅ በእውነተኛ ማንነቱ መኖር እስካልቻለ ድረስ ህሊናቸው ረፍት አያገኝም፡፡ ሰው ተስፋ ያጣበት ነገር ፈላስፋን አንገቱን ያስደፋዋል፤ ከትካዜውም አይመለስም፡፡ ፈላስፋ ሰው ከሀዘኑ፣ ከጭንቀቱ፣ ከችግሩ የሚያወጣ እውቀት እስካላገኘ ድረስ የሚበላውን፣ የሚለብሰውን፣ የሚኖርበትን፣ ወዘተ እስኪረሳ ድረስ በሀሳብ ይናወዛል፡፡
የሰው ልጅ ተስፋ ማጣት ጩኸት በቀንም በሌሊትም በጆሮው ያቃጭልበታል፣ «ምን ልሁን? ተስፋ ቆረጥሁ፣ ታደገኝ እያለ የሚጠራው ይመስለዋል፤ ነፍሱ በህዝቡ ሰቆቃ መሃል ሁና ትዋትታለች፡፡ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ሥርዓቶች በሰው ልጅ ላይ የሚያደርሱት በደል መታገስ የሚችልበት ጉልበት የለውም - ነፍሱ ከተበደሉት ጋር ናት - ሲያለቅሱ ታለቅሳለች፣ ሲታራዙ፣ ሲራቡ፣ ሲሰደዱ አብራቸው ትሰደዳለች፡፡
3.ፈላስፋነት አማጺነት ነው፡፡ፈላስፋ መጥፎ ሥርዓት ላይ አማጺ ነው፡፡ ተፈትኖና ተመርምሮ ባልተረጋገጠ አስተሳሰብና እምነት ጋር አብሮና ተመሣስሎ ላለመኖር እንቢተኛ ነው፡፡ በአጓጉል ማኀበራዊ ሥርዓቶች ተጨፍልቆ ላለመኖርና ራሱን ነፃ ለማውጣት ይጥራል፣ በራሱ ህሊና ለመምራትና የራሱን ማንነት ይዞ ለመገኘት ህሊናው በማይቀበላቸው እምነቶችና አስተሳሰቦች ላይ ያምፃል፡፡ ህሊናውንና ማንነቱን አሳልፎ ሳይሰጥ በተረዳውና በአመነው ነገር ላይ ብቻ ህይወቱን ለመምራት የስብዕና ጥንካሬ ያለው ፈላስፋ ነው፡፡
4.ፈላስፋ ራሱን የሚቀድስ ሰው ነው፡፡ ግለሰቦችና ማኅበራዊ ሥርዓቶች ከሚያደርሱት በደል ራሱን በእውቀት እያበቃ ተካፋይ ላለመሆን የእውነት መንገድን እየፈለገ የሚኖርና ከህብረተሰብ እድፍ ራሱን የሚያነፃ ፈላስፋ ነው፡፡ ስሜታዊነትን፣ አድሏዊነትንና ወገንተኛነትን ከህይወቱ በማስወገድ ስብዕናውን የሚቀድስና በእውቀት የቅድስና ህይወት መኖር የሚችል ፈላስፋ ነው፡፡ፈላስፋ ምድራዊ ለሆነው ማንነት (ለሥጋዊ ደስታ፤ ለክብር፣ ለዝናና ለሐብት) ብሎ ህሊናውን የማይሸጥ እና ላመነበት ነገር እስከ ሞት ፅዋ ድረስ የሚጋፈጥ ነው።
ረ/ፕሮፌሰር ዋለልኝ እምሩ
@zephilosophy
BY ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy
Share with your friend now:
tgoop.com/Zephilosophy/1109