tgoop.com/tseomm/6529
Last Update:
+ ከእነሆኝ እስከ እነኋት +
ማርያምና ሙሴን ምን አገናኛቸው?
ሰሞኑን ‘ድንግል ማርያም ቤዛ ትባላለች ወይንስ አትባልም?’ በሚለው ተዋስኦ ላይ በበርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ‘ሙሴን በቍጥቋጦው በታየው በመልአኩ እጅ እግዚአብሔር ሹምና ቤዛ አድርጎ ላከው’ የሚለው ከሌሎች ጥቅሶች ጋር እንደ አንድ ማስረጃ ‘ሙሴ ቤዛ ከተባለ ድንግል ማርያም እንዴት አትባልም?’ ተብሎ ሲጠቀስ ሰንብቶአል፡፡ [ቤዛ የሚለው ቃል መጽሐፍ ቅዱሱ በተጻፈበት የግሪክ ቋንቋ ‘Iytroten /ransom-bringer, redeemer/’ በግእዙ መድኅን በእንግሊዝኛው deliverer ተብሎ ተተርጉሞአል] (ሐዋ. 7፡35) የነገሩ ተቃዋሚዎች ደግሞ ታዲያ ‘ምን ያገናኘዋል? የማይገናኝ ነገር አታገናኙ! ሙሴ ቤዛ ተባለ እንጂ ማርያም ቤዛ ተባለች ወይ?’ ብለው ሲከራከሩና ሲሳለቁ ነበር፡፡ ስለዚህ ጉዳዩን የበለጠ ማብራራት ግድ ይላል፡፡
በመጀመሪያ ‘ያ እንዲህ ከሆነማ ይሄ እንዴት አይሆንም’ የሚለው የሙግት አገባብ እኛ የፈጠርነው አገላለጽ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱሳዊ የአመክንዮ ቅርጽ ነው፡፡ በረበናተ አይሁድ ዘንድ አገባቡ qal va chomer (የቀላልና ከባድ ንጽጽር) የሚባል ሲሆን ሁለት ክስተቶችን ግራና ቀኝ አስቀምጦ አንዱን አቃላይ ሌላውን አክባጅ (fortiori) መንገድ የሚከተል የረበናት አመክንዮ (rabbinic logic) ነው፡፡
ይህንን የሙግት ስልት የናዝሬቱ ረቢ መድኃኔዓለም ክርስቶስም ከፈሪሳውያን ጋር ሲነጋገር በሚገባ ተጠቅሞበታል፡፡ ‘የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ’ በማለቱ በተቃወሙት ጊዜ ክርስቶስ እንዲህ ሲል ጠይቆአቸው ነበር፡፡
በመዝሙረ ዳዊት ፦ ‘እኔ ግን፦ አማልክት ናችሁ፥ ሁላችሁም የልዑል ልጆች ናችሁ አልሁ’ ተብሎ ተጽፎአል፡፡ (መዝ. 83፡6) ጌታችን ይህንን እውነታ ተጠቅሞ እንዲህ አላቸው፡፡
‘ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ እኔ፦ አማልክት ናችሁ አልሁ ተብሎ በሕጋችሁ የተጻፈ አይደለምን? መጽሐፉ ሊሻር አይቻልምና እነዚያን የእግዚአብሔር ቃል የመጣላቸውን አማልክት ካላቸው፥የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ስላልሁ እናንተ አብ የቀደሰውን ወደ ዓለምም የላከውን፦ ትሳደባለህ ትሉታችሁን?’ (ዮሐ. 10፡35-36)
ጌታ በዚህ ቦታ ላይ ሁለት ነገሮችን እንደ ቀላልና ከባድ አድርጎ አነጻጸረ፡፡ በመዝሙር ካህናትና ሌዋውያን ‘አማልክት ፣ የልዑል ልጆች ’ ተብለው ከተጠሩ አብ የቀደሰኝን ፣ ወደ ዓለም የላከኝ እኔን የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ስላልኩ እንዴት ‘ትሳደባለህ ትሉኛላችሁ’ ብሎ ትንሹን የካህናት አማልክት መባል ከእርሱ የእግዚአብሔር ልጅ መባል ተገቢነት ማስረገጫ አደረገው፡፡
ጌታችን ይህንን የትርጓሜ አመክንዮ በሌላ ጊዜም ደጋግሞታል ፦
‘ከእናንተ አንድ በግ ያለው በሰንበት በጉድጓድ ቢወድቅበት፥ ይዞ የማያወጣው ሰው ማን ነው? እንግዲህ ሰው ከበግ ይልቅ እንደምን አይበልጥም!’ ሲል ትንሹን በግ ከትልቁ ሰው ጋር አነጽጽሮአል ፡፡ (ማቴ. 12፡11-12)
‘እንኪያስ እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠት ካወቃችሁ፥ በሰማይ ያለው አባት ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸው?’ ብሎ ትንሹን የምድር ወላጆችን ሥጦታ ከታላቁ የሰማያዊ አባት ሥጦታ ጋር አነጻጽሮአል፡፡ (ሉቃ. 11፡13)
የኦሪት ምሁሩ ቅዱስ ጳውሎስም በዚሁ ስልት ‘የሙሴን ሕግ የናቀ ሰው ሁለት ወይም ሦስት ቢመሰክሩበት ያለ ርኅራኄ ይሞታል ፤ የእግዚአብሔርን ልጅ የረገጠ ያንንም የተቀደሰበትን የኪዳኑን ደም እንደ ርኵስ ነገር የቆጠረ የጸጋውንም መንፈስ ያክፋፋ፥ እንዴት ይልቅ የሚብስ ቅጣት የሚገባው ይመስላችኋል?’ ብሎ ትንሹን ሕገ ሙሴን ከትልቁ ደመ ክርስቶስ ጋር አነጻጽሮ ሞግቶአል፡፡ (ዕብ. 10፡29)
ብሉይ ጠቅሶ ለሐዲስ ማስረጃ ማድረግ ፣ የሚያንሰውን ጠቅሶ ለሚበልጠው መከራከሪያ የማድረግ አመንክዮ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተገኘ logical method እንጂ ‘ምኑን ከምኑ’ የሚያሰኝ ነገር አይደለም፡፡ ይህ ዓይነቱ አነጋገር አዲስ የሚሆንበት ሰው ለመጽሐፍ ቅዱስ አዲስ የሆነ ብቻ ነው፡፡
ሙሴና ድንግል ማርያምን ምን አገናኛቸው? ለሚልም ሰው የሙሴ ትንሽነትና የማርያም ትልቅነት ‘ሙሴ ቤዛ ከተባለ እሷ ለምን አትባልም?’ ብሎ ለመሟገት ሲሆን በደንብ ይገናኛሉ፡፡ ሙሴና ማርያምን በአንድ ወገን ለመነጻጸር የሚያስችል ደግሞ ብዙ ነገር መጥቀስ ይቻላል፡፡
የእግዚአብሔር ቃል የተጻፈበትን ጽላት የታቀፈ ሙሴ ቤዛ ከተባለ የእግዚአብሔርን ቃል ራሱን የታቀፈች ድንግል እንደምን ቤዛ አትባልም? የፋሲካውን በግ አሳርዶ መቃኑና ጉበኑን የቀባው ሙሴ ቤዛ ከተባለ የፋሲካውን በግ የወለደች ድንግል እንደምን ቤዛ አትባልም?
እውነት ነው ሙሴ በእስራኤል መዳን ላይ ወሳኝ ሰው ነበርና ቤዛ መባል ይገባዋል፡፡ በሲና ተራራ እግዚአብሔር በመልአክ የተነገረውን ቃል ሰምቶ ወደ ፈርኦን ሔዶ የታገለ ፣ ብዙ የተሟገተ ፣ እስራኤልን መርቶ ከግብፅ ያወጣ ሙሴ ቤዛ ቢባል አያንስበትም፡፡ በመላኩ ብሥራት ‘እነሆኝ የጌታ ባሪያ’ ብላ ራስዋን አሳልፋ ለፈጣሪ የማዳን እቅድ የሠጠችው ድንግል ማርያም ከሙሴ በላይ ዋጋ አልከፈለችምን?
አዎ ሙሴ ለተጠማ ሕዝብ ድንጋይ በበትር መትትቶ ውኃ አፍልቆ አጠጥቶ ነበር፡፡ ‘ያ ዓለት ክርስቶስ ነበረ’ የተባለለት ልጅዋ በጦር ሲወጋና ሕይወት የሚሠጥ ደሙ ሲፈስስ ያየችው ድንግልስ ከሙሴ አትበልጥምን? ሙሴ ዓለቱን በበትር ሲመታ አልሳሳም ነበረ፡፡ ልጅዋ በበትር ሲመታ በነፍስዋ ሰይፍ ያለፈው ድንግል አትበልጥምን? ባሕር ከከፈለና ካሻገረው ሙሴ ይልቅ የድንግልናዋን ባሕር ሳይከፍል ዓለምን ያሻገረውን ጌታ የወለደችው ድንግል አትበልጥምን?
ሙሴ ራሱ ያወጣውን ሕገ ኦሪት እንኳን መጠበቅ አቅቶት ከከነአን ቀርቶአል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቆስጠንጢኖስ ይህንን ሲያብራራ ‘ከማርያም በቀር ዐሠርቱ ቃላትን የፈጸመ ማንም የለም’ ‘ወባሕቱ አልቦ ዘፈጸመ ዐሠርተ ቃላተ ዘእንበለ ማርያም ድንግል’ ብሏል፡፡ (መጽሐፈ ብርሃን ዘጸሐፈ አፄ ዘርዐ ያዕቆብ 85) ለሙሴ የተገባ ‘ቤዛ’ የሚል ቃል ለእርስዋ አይገባትም ሲሉን የማንሰማው ለዚህ ነው፡፡
ከመጽሐፍ ቅዱስ ብሉይ ኪዳንን ቀድዶ ጥሎ ፣ የክርስቶስን አካል ጥላ ቢስ አድርጎ ከሚረዳ ሰው በቀር የሙሴና የማርያም ንፅፅር ለሁሉ ግልፅ ነው፡፡ ቤዛ መባሉን ይዘን ከሙሴ ብቻ ጋር አነጻጸርናት እንጂ እርስዋ እንኳን በእኛ ዓይን ባሕር የከፈለች የወንድሙ የአሮን በትር ፣ በ‘ንሴብሖ’ ፈንታ ‘ታዓብዮ’ ያለች ማርያም ፣ የእግዚአብሔር ቃል የወረደባት የሲና ተራራ ፣ የቃሉ ሰሌዳ ጽላት ፣ የመብራት ማቆሚያው መቅረዝ ፣ የጽላቱ ማደሪያ ታቦት ፣ የዕጣኑ መሠዊያም ፣ ደብተራ ኦሪትም እርስዋ ናት፡፡ Typology ከማይገባቸው ሰዎች ጋር መነጋገር ሆነብን፡፡
ሙሴ ለእስራኤል ቤዛ የተባለው እግዚአብሔር እስራኤልን አልተቤዠም ለማለት አይደለም፡፡ የፈጣሪን ቦታ ለመተካት ወይም ለመገዳደርም አልነበረም፡፡ የእግዚአብሔር እስራኤልን የማዳን ሥራ ላይ ሙሴ በቀዳሚነት ስለታዘዘና ሕይወቱን ስለሠጠ ነው፡፡ ይግረማችሁና ‘ሕዝቡም በእግዚአብሔርም በባሪያውም በሙሴ አመኑ’ ተብሎ ተጽፎአል፡፡ (ዘጸ.
BY ኦርቶዶክሳዊ መጻሕፍት እና ጽሑፎች Tsegaye kiflu
Share with your friend now:
tgoop.com/tseomm/6529