tgoop.com/tseomm/6494
Last Update:
"የመስቀል በዓል የጣዖት በዓል ነው” ያለውን ግለሰብ ፍርድ ቤት በነጻ ዋስ ማሰናበቱ ተገለጸ !
ሚያዝያ 7 ቀን 2017 ዓ.ም [ተሚማ/ አዲስ አበባ]
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት በወላይታ ዞን ኪንዶ ዲዳዬ ወረዳ አቶ መርክነህ መጃ የተባለ ግለሰብ ሰኞ መስከረም 5 ቀን 2017 ዓ.ም በግል የፌስቡክ ገጻቸው ላይ “የመስቀል በዓል እንግዲያውስ እስከተነሳ ድረስ እንነጋግርበት” በማለት የመስቀል በዓልን ከጣዖት አምልኮ ጋራ አገናኝተው የጥላቻ ንግግር በመጻፋቸው ፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የወላይታ ሀገረ ስብከት ክስ መስርቶ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መብት ለማስከበር ግለሰቡን በሕግ ጥላ ሥር እንዲቆይ በማድረግ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
ግለሰቡም በዋስትና ተለቅቆ በውጭ ሆኖ ክሱን ሲከታተል የቆየ ሲሆን በመጋቢት 30 ቀን 2017 ዓ.ም የወረዳው ፍ/ቤት በዋለው ችሎት ተከሳሹን በነጻ ማሰናበቱን በመግለጹ ሀገረ ስብከቱ የሰውና የሰነድ ማስረጃ አቅርበን ሳለ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መብት አልተከበረም ሉዓላዊነቷም ተደፍሯል በማለት ይግባኝ ማለቱን የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም ቦክቻ ኤንጋ ለተዋሕዶ ሚዲያ ማዕከል አሳውቀዋል፡፡
ክቡር ሥራ አስኪያጁ አክለውም ።፤ ግለሰቡ “የመስቀል በዓል በብዙ አቅጣጫ ከጣኦት አምልኮ ጋር አያይዘው የሚጠቀሙ ግለሰቦች ስላሉ ለቤተ ክርስቲያን አደገኛ ስለሆነ ፤ በዚህ በዓል እግዚአብሔር አይደለም የሚከበረው” ያሉ እና “ገና ከመነሻው የጣኦት አምልኮ የተካተተበት ነው” በማለት በታሪክም በጽሑፍም ያለውን ማስረጃ የሌለ አድርገው ቅድስት ቤተክርስቲያን የማታስተምረውን እንደምታስተምር ፣ የማትቀበለውን እንደምትቀበል አድርገው የጥላቻ እና የተሳሳተ ንግግር በማኅበራዊ ገጻቸው ያስተላለፉ ሲሆን ይሄንንም በምሳሌ ብለው ሲያስረዱ “እንደሚሉት ንግሥት እሌኒ መስቀሉን በእሳት ጭስ ተመርታ ካገኘች በኋላ የምስጋና ጭስ ላስገኛት አካል አቅርባለች በማለት ለጭሱ የሚያመልኩም አሉና፡፡” በማለት ከእውነት የራቀ የተሳሳተ መረዳታቸውን በአደባባይ አስተላልፈው ሳለ የወረዳው ፍ/ቤት በነጻ በመልቀቁ ቅሬታዋን ቅድስት ቤተክርስቲያን የገለጸች ሲሆን መንግሥት በልዩ ትኩረት ሊከታተለው እንደሚገባ እያስገነዘብን በቀጣይ ፍትሕ እንደምናገኝ በልበ ሙሉነት እየተማመንን ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ የተጠየቀ መሆኑን እንገልጻለን በማለት አያይዘውም የጎጮ ቅዱስ ጊዮርጊስ ይዞታም ከዚሁ ወረዳ በይግባኝ ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርቦ ውሳኔ ማግኘቱ ይታወሳል ብለዋል።
የመስቀል ክብረ በዓልን ዩኔስኮ [Commemoration feast of the finding of the True Holy Cross of Christ] በማለት በዓለም ቅርስነት መመዝገቡን ኅዳር 25 ቀን 2006 ዓ.ም በኢንታንጀብል [መንፈሳዊ] ባህላዊ ቅርሶች ጥበቃና ክብካቤ ላይ የሚሠራው ኮሚቴው ስምንተኛውን ጉባኤ በአዘርባጃኗ ባኩ ከተማ ባደረገበት ጊዜ መመዝገቡን ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው፡፡
BY ኦርቶዶክሳዊ መጻሕፍት እና ጽሑፎች Tsegaye kiflu
Share with your friend now:
tgoop.com/tseomm/6494