tgoop.com/tseomm/6289
Last Update:
እንደ ሁኔታው ለብቻው ልመለስበት እችላለሁ) በጣም የተለያዩ ሀሳቦች ናቸው። እንዲህ ያለው ችግር ቀደም ብሎም የነበረ ችግር ነው። ስለዚህ አሁንም ለመርታት በሚፈልግ ልቡና ውስጥ ሆኖ ጥቅሶችን ከዐውዳቸው ነጥሎ አውጥቶ መጠቀም ችግርን ያባብስ እንደሆን እንጂ መፍትሔ ሊሆን አይችልምና ከዚህም መጠበቅ ተገቢ ነው።
4) ከመጠራጠር አለመጀመር
መና/ፍቃን ሀሳብ እና ጥያቄ ሲያነሱ የእነርሱን አመክንዮ እና ፍረጃ ሰምቶ ነባር ትምህርቶችን ወይም ምንጮቻችን ከመጠራጠር መጀመር በጣም አደገኛ ነገር ነው። ለምሳሌ ሳጥናኤል እኔ ፈጠርኳችሁ ባለ ጊዜ በጥርጥር የጀመሩት እውነት በተገለጠ ጊዜ ከእርሱ ጋር አብረው ወድቀው የሚያስቱ መናፍስት ሆኑ እንጂ ሲመለሱ አላየናቸውም። እውነቱን ባያውቁም በያለንበት እንቁም ባለው በቅዱስ ገብር ኤል ቃል ጥርጥሩን ሳያስገቡ የጸኑት ግ ን በኋላ እግዚአብሔር እውነቱን ገልጾላቸዋል። ይህ የመጀመሪያው የፍጥረት ፈተና የሚያስረዳን ከመጠራጠር መጀመር ምን ያህል አደገኛ መሆኑን ብቻ ሳይሆን መንገዱ ዲያብሎሳዊ መሆኑን ነው። በሳይንስ ከመጠራጠር መጀመር ወደ ዕውቀት ይወስዳል ከሚባለው በተቃራኒ በሃይማኖት በመጠራጠር አለመጀመር መሠረታዊ ጉዳይ ሆኖ እናገኘዋለን ማለት ነው።
በዚሁ መንገድ ካየን አንዳንድ የግእዝ ምንጮቻችን ከሌላ ሀገር ምንጮች ስናነጻጽር በቀጥታ ላይገጥሙልን ይችላሉ። ለምሳሌ ያህል ገድለ ጊዮርጊስን ስንመለከት ሰማዕቱን ያሰቃየውን ንጉሥ ዱድያኖስ ይለዋል። በሌላው ሀገር ግን ያሉት ምንጮች በሙሉ ደግሞ ንጉሡን ዲዮቅልጥያኖስ ይሉታል። ይህ በመሆኑ የእኛ ምንጭ ስሐተት ነው ልንል አንችልም። እኔ እንኳ በአቅሜ በአደረግሁት ፍለጋ አንድ ጥናት ላይ የጥንት ምንጮች ዱድያኖስ ይሉ እንደነበር አግኝቻለሁ። ስለዚህ ይህ ስም ምንጫችን ስሐተት መሆኑን ሳይሆን ምንጫችንን ወይም አቀባይ ቋንቋችንን እንድንመረምር እና የእኛ ቅጂ ከቀዳማውያን ምንጮች መሆኑን ይጠቁማል እንጂ ልዩ መሆኑ ስሕተት መሆኑን ሊያሳይ አይችልም ማለት ነው።
በገድለ ተክለ ሃይማኖት ላይ ያለው የሞቱበትን በሽታ እንደመስቀሌ እቆጥርልሃለሁ የሚለውን ሀሳብ ስሑታኑ ባነሡበት መንገድ ተመልክቶ ከመጠራጠር ከመጀመር ወደ ገድሉ ጠልቆ ገብቶ ምክንያቱን ከማጥናት መጀመር ከብዙ በሽታ ይፈውሳል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ገድሉን ስንመለከት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ትልቁ ፍላጎታቸው የደም ሰማዕትነትን ማግኘት ነበር። ዘመኑ ደግሞ ያንን አልፈቀደላቸውም። ስለዚህ ጌታ በበሽታ የገጠማቸውን ተጋድሎ እንደ ሰማዕትነት ወይም መስቀል እንደሚቆጥርላቸው ቃልኪዳን ገባላቸው ይላል እንጂ መና/ፍቃኑ የሚሉትን ወይም ሊሉ የሚፈልጉትን ገድሉ በፍጹም አይልም።
በገድለ ቅዱሳንና በገድለ ቅዱሳን መጽሐፍ መካከል ልዩነት እንኳ ቢኖር ወደ ቀዳማይ ምንጭ በሚደረግ ጥናት ይስተካከላል እንጂ ገድለ ቅዱሳንን ወደ መጠራጠር ሊወስድ አይችልም። በርግጥ የሰው አእምሮ ውሱን ስለሆነ ለእንዲህ ያለ ፈተና ተደጋግሞ ሊወድቅ ይችላል። እንዲህ ያሉትን ነገሮች ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስም ያስረዳል። ለምሳሌ ያህል በሰማርያ እጅ ከባድ ረሀብ ተነሥቶ ሁለት ሴቶች ልጆቻቸውን ቀቅለው ለመብላት ከተስማሙና የአንዲቱን ከበሉ በኋላ ሁለተኛ ልጇን ስትደብቅ በተፈጠረው ክርክር ንጉሡ ስሞቶ በኤልሣዕ ላይ ተቆጥቶ ነበር። በኋላ ላይ ግን “የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ነገ በዚህ ጊዜ በሰማርያ በር አንድ መስፈሪያ መልካም ዱቄት በአንድ ሰቅል፥ ሁለትም መስፈሪያ ገብስ በአንድ ሰቅል ይሸመታል አለ። ንጉሡም በእጁ ተደግፎ የነበረ አለቃ ለእግዚአብሔር ሰው መልሶ፦ እነሆ፥ እግዚአብሔር በሰማይ መስኮቶች ቢያደርግ ይህ ነገር ይሆናልን? አለው። እርሱም፦ እነሆ፥ በዓይኖችህ ታየዋለህ፥ ከዚያም አትቀምስም አለ” /2ኛ ነገ 7/ ተብሎ እንደተጻፈ ንጉሡ በመጠራጠሩ ምክንያት በሕይወቱ እንዲቀጣ ሆኗል። ስለዚህ ከመጠራጠር መጀመር ውጤቱ አደገኛ መሆኑን መረዳት እና በእምነት ጸንቶ የማያውቁትን ለማውቅ መጣር ተገቢነት ይኖረዋል ማለት ነው። ለዛሬው በእነዚሁ ልፈጸም። ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን።
✍️መምህር ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ እንደጻፉት
BY ኦርቶዶክሳዊ መጻሕፍት እና ጽሑፎች Tsegaye kiflu
Share with your friend now:
tgoop.com/tseomm/6289