Telegram Web
ወደ በዓቱም ያ ረድእ በገባ ጊዜ በምድር ላይ ሰግዶ እንዳረፈ አባ ዮሐንስን አገኘውና ታላቅ ልቅሶን በላዩ አለቀሰ ከዚያም በኋላ ወደ መነኰሳቱ መንደር ፈጥኖ በመሔድ ቅዱስ አባ ዮሐንስ ሐፂር እንደ አረፈ ነገራቸው ። እነዚያም መነኰሳት አክብረው ገንዘው ሥጋውን ተሸክመው ወስደው በቦታቸው አኖሩት።

የደረቀ ዕንጨት ተክሎ በአበቀለበት ላይ በሠራት የራሱ በሆነች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ልጆቹ ከዚህ አፍልሰው ወስደው እስከ አኖሩት ድረስ በዚያ ኖረ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ነቢይ_ኤልሳዕ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የስሙ ትርጓሜ ጠባቂና አዳኝ የሆነ የታላቅ ነቢይ የኤልሳዕ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

እርሱም አሜሁላ ከሚባል አገር ከይሳኮር ነገድ ነው ብዙ ትንቢትን ተናግሮአል ብዙ ተአምራትንም አድርጓል። የኢያሪኮም ሰዎች ኤልሳዕን #ጌታችን እንደምታያት የዚች አገር ኑሮዋ ያማረ የተወደደ ነው የአገሩ ውኃ ግን ክፉ ነው ሴቶች ሲጠጡት ይመክናሉ አሉት ቅዱስ ኤልሳዕም ጨው ጨምራችሁ አዲስ ሸክላ አምጡልኝ አላቸው እነርሱም አመጡለት ።

ቅዱስ ኤልሳዕም ወደ ውኃው ምንጭ ሒዶ ያንን ጨው በውስጡ ጨመረውና #እግዚአብሔር እንዲህ አለ እርሱን ከመጠጣት የተነሣ የሚሞት እንዳይኖር የሚመክንም እንዳይኖር ይህን ውኃ ለውጥኩት አለ አላቸው ።

ከዚያችም ቀን በኋላ ቅዱስ ኤልሳዕ እንደተናገረ እስከ አሁን ድረስ ያ ውኃ ተለወጠ። የዚህ የነቢይ ኤልሳዕ ተአምራቱ ብዙ ነው የሶርያውን ሰው ንዕማንን ከለምጹ ያነጻው እርሱ ነው ሁለት ሙታንን አንዱን በሕይወት ሳለ ሌላውንም ከሞተ በኋላ አስነሥቷል። የትንቢቱንም ወራት ፈጽሞ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት_20)
🌹#የጥቅምት_20_ግጻዌ

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_20_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዕብራውያን 12
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹¹ ቅጣት ሁሉ ለጊዜው የሚያሳዝን እንጂ ደስ የሚያሰኝ አይመስልም፥ ዳሩ ግን በኋላ ለለመዱት የሰላምን ፍሬ እርሱም ጽድቅን ያፈራላቸዋል።
¹² ስለዚህ የላሉትን እጆች የሰለሉትንም ጉልበቶች አቅኑ፤
¹³ ያነከሰውም እንዲፈወስ እንጂ እንዳይናጋ፥ ለእግራችሁ ቅን መንገድ አድርጉ።
¹⁴ ከሰው ሁሉ ጋር ሰላምን ተከታተሉ ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ፥ ያለ እርሱ ጌታን ሊያይ የሚችል የለምና።
¹⁵ የእግዚአብሔር ጸጋ ለማንም እንዳይጎድለው፥ ብዙዎቹም የሚረክሱበት አንድ መራራ ሥር ወደ ላይ በቅሎ እንዳያስጨንቅ፥ ሴሰኛም የሚሆን እንዳይገኝ፥
¹⁶ ወይም ስለ አንድ መብል በኵርነቱን እንደ ሸጠ እንደ ዔሳው ለዚህ ዓለም የሚመች ሰው እንዳይሆን ተጠንቀቁ።
¹⁷ ከዚያ በኋላ እንኳ በረከቱን ሊወርስ በወደደ ጊዜ እንደ ተጣለ ታውቃላችሁና፤ በእንባ ተግቶ ምንም ቢፈልገው ለንስሐ ስፍራ አላገኘምና።
¹⁸ ሊዳሰስ ወደሚችል ወደሚቃጠልም እሳት ወደ ጭጋግም ወደ ጨለማም ወደ ዐውሎ ነፋስም ወደ መለከት ድምፅም ወደ ቃሎችም ነገር አልደረሳችሁምና፤
¹⁹ ያንም ነገር የሰሙት ሌላ ቃል እንዳይጨመርባቸው ለመኑ፤
²⁰ እንስሳ እንኳ ተራራውን ቢነካ ተወግሮ ይሙት የምትለውን ትእዛዝ ሊታገሡ አልቻሉምና፤
²¹ ሙሴም፦ እጅግ እፈራለሁ እንቀጠቀጥማለሁ እስኪል ድረስ የሚታየው እጅግ የሚያስፈራ ነበር፤
²² ነገር ግን ወደ ጽዮን ተራራና ወደ ሕያው እግዚአብሔር ከተማ ደርሳችኋል፥ ወደ ሰማያዊቱም ኢየሩሳሌም፥ በደስታም ወደ ተሰበሰቡት ወደ አእላፋት መላእክት፥
²³ በሰማያትም ወደ ተጻፉ ወደ በኵራት ማኅበር፥ የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር፥ ፍጹማንም ወደ ሆኑት ወደ ጻድቃን መንፈሶች፥
²⁴ የአዲስም ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፥ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል።
²⁵ ለሚናገረው እምቢ እንዳትሉ ተጠንቀቁ፤ እነዚያ በምድር ላስረዳቸው እምቢ ባሉ ጊዜ ካላመለጡ፥ ከሰማይ ከመጣው ፈቀቅ የምንል እኛስ እንዴት እናመልጣለን?
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 4
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶ እንደ ሰዎች በሥጋ እንዲፈረድባቸው በመንፈስ ግን እንደ እግዚአብሔር እንዲኖሩ ስለዚህ ምክንያት ወንጌል ለሙታን ደግሞ ተሰብኮላቸው ነበርና።
⁷ ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦአል። እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፥
⁸ ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ፤ ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ።
⁹ ያለ ማንጐራጐር እርስ በርሳችሁ እንግድነትን ተቀባበሉ፤
¹⁰ ልዩ ልዩን የእግዚአብሔርን ጸጋ ደጋግ መጋቢዎች እንደ መሆናችሁ፥ እያንዳንዳችሁ የጸጋን ስጦታ እንደ ተቀበላችሁ መጠን በዚያው ጸጋ እርስ በርሳችሁ አገልግሉ፤
¹¹ ማንም ሰው የሚናገር ቢሆን፥ እንደ እግዚአብሔር ቃል ይናገር፤ የሚያገለግልም ቢሆን፥ እግዚአብሔር በሚሰጠኝ ኃይል ነው ብሎ ያገልግል፤ ክብርና ሥልጣን እስከ ዘላለም ድረስ ለእርሱ በሚሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 20
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³¹ ስለዚህ ሦስት ዓመት ሌሊትና ቀን በእንባ እያንዳንዳችሁን ከመገሠጽ እንዳላቋረጥሁ እያሰባችሁ ትጉ።
³² አሁንም ለእግዚአብሔርና ያንጻችሁ ዘንድ በቅዱሳንም ሁሉ መካከል ርስትን ይሰጣችሁ ዘንድ ለሚችል ለጸጋው ቃል አደራ ሰጥቻችኋለሁ።
³³ ከማንም ብር ወይም ወርቅ ወይም ልብስ አልተመኘሁም፤
³⁴ እነዚህ እጆቼ በሚያስፈልገኝ ነገር ለእኔና ከእኔ ጋር ላሉት እንዳገለገሉ እናንተ ታውቃላችሁ።
³⁵ እንዲሁ እየደከማችሁ ድውዮችን ልትረዱና እርሱ ራሱ፦ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው እንዳለ የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ በሁሉ አሳየኋችሁ።
³⁶ ይህንም ብሎ ተንበርክኮ ከሁላቸው ጋር ጸለየ።
³⁷ ሁሉም እጅግ አለቀሱ፥ ጳውሎስንም አንገቱን አቅፈው ይስሙት ነበር፤
³⁸ ይልቁንም፦ ከእንግዲህ ወዲህ ፊቴን አታዩም ስላላቸው ነገር እጅግ አዘኑ። እስከ መርከብም ድረስ ሸኙት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_20_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"አርውዮ ለትለሚሃ። ወአሥምሮ ለሚእረራ። ወበነጠብጣብከ ትበቊል ተፈሢሓ። መዝ 64፥10።

#ትርጉም፦ “ትልምዋን ታረካለህ፥ ቦይዋንም ታስተካክላለህ፤ በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ፥ ቡቃያዋንም ትባርካለህ።” መዝ 64፥10።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_20_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 4
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁷ በነቢዩ በኤልሳዕ ዘመንም በእስራኤል ብዙ ለምጻሞች ነበሩ፥ ከሶርያዊው ከንዕማን በቀር ከእነርሱ አንድ ስንኳ አልነጻም።
²⁸ በምኵራብም የነበሩ ሁሉ ይህን ሰምተው ቍጣ ሞላባቸው፥ ተነሥተውም ከከተማ ወደ ውጭ አወጡት፥
²⁹ ይጥሉትም ዘንድ ከተማቸው ተሠርታባት ወደ ነበረች ወደ ተራራው አፋፍ ወሰዱት፤
³⁰ እርሱ ግን በመካከላቸው አልፎ ሄደ።
³¹ ወደ ገሊላ ከተማም ወደ ቅፍርናሆም ወረደ። በሰንበትም ያስተምራቸው ነበር፤
³² ቃሉ በሥልጣን ነበርና በትምህርቱ ተገረሙ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 🌹
የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የ #ማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ዮሐንስ ሐፂርና የዕረፍት በዓል፣ የነቢዩ የቅዱስ ኤልሳዕ የመታሰቢያ በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችን ይሁንልን።  
🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_21

#አንድ_አምላክ_በሆነ_በአብ_በወልድ_በመንፈስ_ቅዱስ ስም
ጥቅምት ሃያ አንድ በዚህችም ቀን #እመቤታችን_ተአምራትን_አድርጋ_ሐዋርያው_ማትያስን ከእሥራት ቤት ያወጣችበት፣ #የነቢይ_ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ፣ የማርታና የማርያም ወንድም #የቅዱስ_አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት፣ የቅዱስ አባት #አባ_ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም እረፍት ነው፣ ታላቁ ጻድቅ #አቡነ_አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#እመቤታችን_ለሐዋርያው_ቅዱስ_ማትያስ_ያደረገችለት_ተአምር

በዚህችም ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል #ማርያም ተአምራትን አድርጋ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ማትያስን ከእሥራት ቤት አዳነችው።

የከበሩ ቅዱሳን ወንጌልን በዓለም ዞረው ይሰብኩ ዘንድ ዕጣ ሲጣጣሉ ለቅዱስ ማትያስ ዕጣ የደረሰው ሰውን ወደሚበሉ ሰዎች አገር ነበር፡፡ ይህችም ሀገር እስኩቴስ የተባለች ሩሲያ እንደሆነች የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች ፍንጭ ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስ ማትያስም እነዚህ ሰውን የሚበሉ ሰዎች አገራቸው እንደደረሰ ዐይኑን አውልቀው አሠሩት፡፡ ምግባቸውም የመጻተኛ ሰው ሥጋ ነው፡፡ በልማዳቸው መሠረት መጻተኛን ሰው ገና እንደያዙት ዐይኖቹን ዐውልቀው በእሥር ቤት ያኖሩታል፡፡ እስከ 30 ቀንም ድረስ ሳር እያበሉ ያስቀምጡትና በ30ኛው ቀን አውጥተው አርደው ይበሉታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ማትያስንም በልማዳቸው መሠረት ዐይኖቹን አውልቀው አሠሩት፡፡ ሐዋርያውም በእሥር ቤት ሆኖ በዚያ ላይ ዐይኖቹን ታውሮ ሳለ በጭንቅ ወደ #ጌታችንና ወደ #እመቤታችን ይለምን ነበር፡፡ ነገር ግን #አመብርሃንና ልጇ #መድኃኔዓለም 30ኛው ቀን ሳይፈጸም ሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስን ወደ እርሱ ላኩለት፡፡ ቅዱስ ማትያስም ዐይኑን ፈወሱለትና ማየት ቻለ፡፡

ቅዱስ እንድርያስም በተዘጋው በር በተአምራት ገብቶ አሥርቤቱ ውስጥ ያሉ እሥረኞችን በስውር አውጥቶ ከከተማው ውጭ ካስቀመጣቸው በኋላ ሁለቱ ሐዋርያት ተመልሰው ሰውን ለሚበሉት ሰዎች ተገለጡላቸው፡፡ እነርሱም ይዘው በአንገታቸው ገመድ አግብተው ለ3 ቀን በሀገራቸው ጎዳናዎች ላይ ሁሉ ጎተቱዋቸው፡፡ ሁለቱም ሐዋርያት በጸሎታቸው ከእሥር ቤቱ ምሰሶ ሥር ውኃ አፈለቁና ውኃው ሀገራቸውን ሁሉ እስኪያጥለቀልቅና ሰዎቹንም እስከ አንገታቸው ድረስ እስከሚደርስ ሞላ፡፡ ሁሉም በተጨነቁ ጊዜ ሁለቱ ሐዋርያት በፊታቸው ተገለጡና ‹‹በ #ጌታችን እመኑ ትድናላችሁ›› በማለት ወንጌልን ሰብከውላቸው አሳመኗቸው፡፡ ምሥጢራትንም ሁሉ ገለጡላቸው፡፡ ደግሞም የአራዊት ጠባይን ከሰዎቹ ያርቅላቸው ዘንድ ወደ #ጌታችንና ወደ ተወደደች እናቱ ከጸለዩ በኋላ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አጠመቋቸው፡፡ ያ የአውሬነት ጠባያቸውም ጠፍቶላቸው የዋህ፣ ቅንና ሩኅሩኆቸ ሆኑ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም ሃይማኖትን እያስተማሯቸው 30 ቀን አብረዋቸው ከተቀመጡ በኋላ አገልጋይ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ካህናትንና ዲያቆናትን ሾመውላቸው ወደ ሌላ ሀገር ሄዱ፡፡

ለቅዱሳን ሐዋርያት ሞገሳቸው ጣዕመ ስብከታቸው የኾነች ክብርት #እመቤታችን ለእኛም ትለመነን ለዘላለሙ አሜን!

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ኢዩኤል_ነቢይ

ዳግመኛም በዚህችም ቀን የነቢይ ኢዩኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህም የእስራኤልን ልጆች የሚያስተምርና የሚገሥጻቸው ነበር ስለ #ክርስቶስም በኢየሩሳሌም መኖርና ማስተማር ትንቢት ተናገረ። ደግሞም ስለ መከራው በሐዋርያትና በሰባ ሁለቱ አርድእት በሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ላይ የ #መንፈስ_ቅዱስን መውረድ እንዲህ ሲል ተናገረ።

ከዚህ በኋላ በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ ከመንፈሴ አሳድርበታለሁ ሴቶች ልጆቻችሁና ወንዶች ልጆቻችሁ ትንቢትን ይናገራሉ አለቆቻችሁ ሕልምን ያልማሉ ጎልማሶቻችሁም ራእይን ያያሉ። ሁለተኛም እንዲህ አለ ያን ጊዜ ከተራራው ማር ከኮረብታውም ወተት ይፈሳል በቤተ #እግዚአብሔር አጠገብ ካሉ ከይሁዳ አገሮች ሁሉ ምንጩ ከላይ ወደታች ይፈሳል።

ሙታን በሚነሡ ጊዜ ስለሚሆነው የፍርድ ሰዓት እንዲህ አለ ፀሐይና ጨረቃ ይጨልማሉ የከዋክብትም ብርሃናቸው ይጠፋል። የትንቢቱንም ወራት አድርሶ #እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በነብዩ ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አልዓዛር የማርታና የማርያም ወንድም

በዚችም ቀን ክብር ይግባውና #ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከሙታን ያስነሣው የቅዱስ አልዓዛር ሥጋው ከቆጵሮስ አገር የፈለሰበት ሆነ።

ከክርስቲያን ነገሥታትም አንዱ ሥጋው በቆጵሮስ እንዳለ በሰማ ጊዜ ከቆጵሮስ ደሴት ወደ ቊስጥንጥንያ አፈለሰው። ሊአፈልሱትም በወደዱ ጊዜ በከበረ የደንጊያ ሣጥን ውስጥ ሁኖ በምድር ውስጥ ተቀብሮ አገኙት በላዩም እንዲህ የሚል ጽሑፍ ነበረ ይህ በመቃብር ውስጥ አራት ቀን ከኖረ በኋላ ከሙታን ለይቶ ላስነሣው ክብር ይግባውና የ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ወዳጁ የሆነ የቅዱስ አልዓዛር ሥጋ ነው።

ይህንንም በአዩ ጊዜ ደስ ተሰኙበት ተሸክመውም ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ወሰዱት ካህናቱም ሁሉ ወጥተው በታላቅ ክብር በመዘመርና በማመስገን ተቀበሉት በአማረ ቦታም አኖሩት በዚችም ቀን በዓልን አደረጉለት።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አልዓዛር ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ዘኢየሩሳሌም

በዚህችም ቀን ለከበረች አገር ኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት የሆነ ቅዱስ አባት አባ ዮሐንስ #እግዚአብሔርን በሚወድ የንጉሥ ሰይፈ አርዕድ ደግሞ ቈስጠንጢኖስ ለሚባል ልጁ በሆነ በንጉሣችን በዳዊት ዘመን አረፈ።

ይህም ቅዱስ ከምስር አገር ታላላቆች #እግዚአብሔርን የሚፈሩ የክርስቲያኖች አባቶች ልጅ ነው። የዲቁና መዓረግንም ለመሾም እስከ ተገባው ድረስ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያስተማሩ በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። ከዚህም በኋላ በዲቁናው ሹመት አገልግሎቱን በአሳመረ ጊዜ የቅስና መዓረግ የሚገባው ሁኖ ቅስና ተሾመ።

በጾም በጸሎት #እግዚአብሔርንም በመፍራት የተጠመደ ሁኖ ድኆችንና ችግረኞችን የሚወዳቸው የሚረዳቸው ሆነ ያን ጊዜ የሐዋርያት የሆነች የጵጵስና ሹመት የምትገባው ሁና በከበረች አገር በኢየሩሳሌም በ #እግዚአብሔር ፈቃድ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ሕዝቡንም በፈሪሀ #እግዚአብሔርና በትሕትና የሚያስተምራቸው ሆነ።

እነርሱም ስለ ቅድስናው እጅግ የሚወዱት ሆኑ መልኩና የአንደበቱ አገላለጥ እንደ #እግዚአብሔር መልአክ ያማረ ነበር። በሹመቱም ጥቂት ዘመናት ከኖረ በኋላ ከመንበረ ሢመቱ እስከ አራቀው ድረስ በላዩ ሰይጣን ምክንያትን አመጣ።

ይህም እንዲህ ነው በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በአባ ማርቆስ ዘመን በግዛቱ ውስጥ ያሉ እስላሞች ስለ ዐመፁበት የኢትዮጵያ ንጉሥ ፈጅቷቸው ነበርና ስለዚህ በግዛቱ ውስጥ በሚኖሩ እስላሞች ላይ ክፉ እንዳያደርግ ለኢትዮጵያ ንጉሥ መልእክት እንዲልክ ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን የምስር ንጉሥ አዘዘው።
አባ ማርቆስም ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥ ስለሚላኩ ሰዎች ከመኳንንቱ ከኤጲስ ቆጶሳቱና ከሀገር ታላላቆች ሽማግሌዎች ጋር ተማክሮ እሊህን ብሩሀን ከዋክብት የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስን የምስር ኤጲስቆጶስ አባ ሳዊሮስን በእውቀታቸው በአስተዋይነታቸውና በቅድስናቸው መረጡአቸው ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥም ይሔዱ ዘንድ ግድ አሏቸው። እነርሱም ታዛዦች ሁነው ወደ ኢትዮጵያ መጡ የኢትዮጵያ ንጉሥም መምጣታቸውን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው እሊህንም ቅዱሳን አባቶች ይቀበሏቸው ዘንድ አሽከሮቹን በቅሎዎችን አስይዞ ላከ በመጡም ጊዜ በታላቅ ደስታ ሰላምታ አቀረበላቸው ከእርሳቸውም ቡራኬን ተቀበለ ታላቅ ክብርንም አከበራቸው ። እነርሱም የሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስን ደብዳቤ ሰጡት እርሱም ተቀብሎ አንብቦ ለሊቀ ጳጳሳቱ ቃል ታዛዥ መሆኑን ገለጠላቸው።

ከዚህም በኋላ ወደ ሀገረ ስብከታቸውና ወደ ሕዝባቸው መመለስን በአሰቡ ጊዜ ስለ ቅድስናቸውና ስለ ትምህርታቸው ጣዕም ስለ ወደዳቸው የተከበረው ንጉሥ መመለስን ከለከላቸው በእርሱ ዘንድ እነርሱ እንደ #እግዚአብሔር መላእክት ሁነዋልና ፊታቸውም እንደ ፀሐይ ያበራል።

ከጥቂት ወራትም በኋላ ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው #እግዚአብሔር በወደደ ጊዜ በላዩ ደዌ ላከበት በዚያውም ደዌ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሱ ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_አላኒቆስ

ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቁ ጻድቅ አቡነ አላኒቆስ ዕረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አላኒቆስ የትውልድ ቦታቸው ሸዋ አንኮበር ሲሆን አባታቸው ንጉሡ ዐፄ ይኩኖ አምላክ ነው፡፡ ንጉሡ አባታቸው ‹‹አግባና መንግሥቴን ይዘህ ተቀመጥ›› ቢላቸው እርሳቸው ግን ንግሥናን በመናቅ እምቢ ብለው ሄደው ከ#እመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቀው ቢለምኗት #እመቤታችን ተገልጣላቸው ‹‹ክፍልህ ምናኔ ነው፣ የአባትህ መንግሥት ያልፋል የልጄ መንግሥት ግን ዘላለማዊ ነው›› አለቻቸው፡፡ ጻድቁም ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ሄደው በዚያው መንኩሰው ገዳሙን እያገለገሉ ተቀመጡ፡፡ ከጸሎታቸው በኋላ ራሳቸውን ወደ ባሕሩ ይጥሉ ነበርና አንድ ቀን እንዲሁ ራሳቸውን ወደ ባሕሩ ሲጥሉ መላእክት አውጥተዋቸዋል፡፡ አቡነ አላኒቆስ ወደ አክሱም እንዲሄዱ ታዘው ከሄዱ በኋላ በዚያም የጽላተ ሙሴ የታቦተ ጽዮን አጣኝ ሆነው 40 ዓመት ተቀምጠዋል፡፡ #እመቤታችንም ተገልጣላቸው በዓታቸውን እንዲያጸኑ ከነገረቻቸው በኋላ ከአክሱም ወጣ ብሎ የሚገኘውን ማይበራዝዮ ገዳምን መሠረቱ፡፡ በዚያም እጅግ አስገራሚ ተአምራትን እያደረጉ ወንጌልን እያስተማሩ አገልግለዋል፡፡

አንድ ቀን መኰንኑ ወደ ሩቅ ቦታ ሲሄድ ቤተሰባቸውን ለ #ንስሓ አባታቸው አደራ ሰጥተው ሄዱ፡፡ የ #ንስሓ አባታቸውም የአቡነ አላኒቆስ ጓደኛ ነበሩ፡፡ መኰንኑም ከሄዱበት ሲመለሱ ሚስታቸው ከአሽከሯ አርግዛ ጠበቀቻቸው፡፡ ‹‹ከማን አረገዝሽ?›› ብለው ጽኑ ግርፋት ቢገርፏት ዋሽታ ‹‹ያረገዝኩት ከንስሓ አባቴ ነው›› አለች፡፡ መኰንኑም መነኩሴውን እገላለሁ ብሎ ሲነሣ መነኩሴውም ወደ አቡነ አላኒቆስ ሄደው አለቀሱ፡፡ አቡነ አላኒቆስም የመኰንኑን ሚስት ቢጠይቋት ባሏን ፈርታ ‹‹አዎ ከመነኩሴው አባት ነው ያረገዝኩት›› አለች፡፡ እሳቸውም ‹‹የተረገዘው ከዚህ መነኩሴ ከሆነ በሰላም ይወለድ፣ ካልሆነ ግን አይወለድ›› ብለው በቃላቸው አስረውና ገዝተው ሸኟቸው፡፡

በግዝታቸው መሠረት ሴቲቱ ድፍን 22 ዓመት ሙሉ ሳትወልድ በጭንቅና በጣር ኖረች፡፡ በአልጋ ላይ ሆና ተጨንቃ ስትኖር በመጨረሻ ለቤተሰቦቿ ተናግራ ወደ አቡነ አላኒቆስ ዘንድ በቃሬዛ ወሰዷትና ይቅርታ ጠይቃ እውነቱን ተናገረች፡፡ እሳቸውም ‹‹#እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ቢሏት 22 ዓመት ሙሉ ተረግዞ የነበረው ልጅ ትልቅ ሰው ሆኖ ጥርስ አውጥቶ፣ ፂም አብቅሎ በሰላም ተወለደ፡፡ እርሱም ከተወለደ በኋላ አባቱ ማን እንደሆነ ተናገረ፡፡ ጻድቁ አባታችንም ልጁን አሳድገውት አስተምረው አመንኩሰውታል፡፡ ስሙንም ተወልደ መድኅን አሉት፡፡ በስሙ የተሠሰራ ቤተ ክርስቲያን በትግራይ ጽንብላ ወረዳ ይገኛል፡፡

ጻድቁ አቡነ አላኒቆስ ሌላም የሚታወቁበት አንድ ግብር አላቸው፡፡ የማይበራዝዮ ገዳማቸው አገልጋይ የሆነው መነኩሴ በሬ ጠምዶ ሲያርሱ አንበሳ ከጫካው ወጥቶ አንዱን በሬ በላው፡፡ መነኩሴውም መጥተው ለአቡነ አላኒቆስ ነገሯቸው፡፡ እሳቸውም ‹‹ጸሎቴን እስክጨርስ ድረስ ወደ ጫካው ሂድና አንበሳውን ‹አላኒቆስ ባለህበት ጠብቀኝ እንዳትንቀሳቀስ ብሎሃል› ብለህ ተናገር›› ብለው ለመነኩሴው ነገሯቸው፡፡

መነኩሴውም እንደታዘዙት ወደ ጫካው ሄደው ጮኸው በሉ የተባሉትን ተናገሩ፡፡ አቡነ አላኒቆስም ጸሎታቸውን ሲጨርሱ ወደ ጫካው ሄደው አንበሳውን የበላውን በሬ አስተፍተውት በሬውን ነፍስ ዘርተውበት ከሞት አስነሥተው ዕለቱን እንዲታረስ አድርገውታል፡፡ አንበሳውንም ገዝተው ወደ ገዳማቸው ወስደው ሰባት ዓመት ውኃ እያስቀዱት እንዲያገለግላቸው አድርገውታል፡፡

አቡነ አላኒቆስ አንበሳውን አስረው ያሳድሩበት የነበረው ዛፍና ውኃ ያጠጡበት የነበረው ትልቅ የድንጋይ ገበታ ዛሬም ድረስ በገዳሙ ይገኛል፡፡ ከ22 ዓመት እርግዝና በኋላ ሴቲቱ ጥርስና ፂም ያለው ልጅ እንድትወልድ ያደረጉበት ትልቅ ጠፍጣፋ ድንጋይም ከነቅርጹ በገዳሙ በግልጽ ይታያል፡፡ ጻድቁ ጥቅምት 21 ቀን ዐርፈው በዚያው በማይባራዝዮ ገዳማቸው ተቀብረዋል፡፡ ጸበላቸው እጅግ ልዩ ነው፣ ያላመነውን ሰው አስፈንጥሮና ገፍትሮ ይጥለዋል እንጂ አያስቀርበውም፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን አባቶች ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት_21 እና #ከገድላት_አንደበት)
🌹#የጥቅምት_21_ግጻዌ🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጥቅምት_21_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሮሜ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁹ ኢየሱስ ጌታ እንደ ሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳስነሣው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤
¹⁰ ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና።
¹¹ መጽሐፍ፦ በእርሱ የሚያምን ሁሉ አያፍርም ይላልና።
¹² በአይሁዳዊና በግሪክ ሰው መካከል ልዩነት የለምና፤ አንዱ ጌታ የሁሉ ጌታ ነውና፥ ለሚጠሩትም ሁሉ ባለ ጠጋ ነው፤
¹³ የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናልና።
¹⁴ እንግዲህ ያላመኑበትን እንዴት አድርገው ይጠሩታል? ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ? ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ?
¹⁵ መልካሙን የምሥራች የሚያወሩ እግሮቻቸው እንዴት ያማሩ ናቸው ተብሎ እንደ ተጻፈ ካልተላኩ እንዴት ይሰብካሉ?
¹⁶ ነገር ግን ሁሉ ለምሥራቹ ቃል አልታዘዙም። ኢሳይያስ፦ ጌታ ሆይ፥ ምስክርነታችንን ማን አመነ? ብሎአልና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ዮሐንስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁵ አሁንም፥ እመቤት ሆይ፥ እርስ በርሳችን እንድንዋደድ እለምንሻለሁ፤ ይህች ከመጀመሪያ በእኛ ዘንድ የነበረች ትእዛዝ ናት እንጂ አዲስ ትእዛዝን እንደምጽፍልሽ አይደለም።
⁶ እንደ ትእዛዛቱም እንሄድ ዘንድ ይህ ፍቅር ነው፤ ከመጀመሪያ እንደ ሰማችሁ፥ በእርስዋ ትሄዱ ዘንድ ትእዛዙ ይህች ናት።
⁷ ብዙ አሳቾች ወደ ዓለም ገብተዋልና እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ እንደ መጣ የማያምኑ ናቸው፤ ይህ አሳቹና የክርስቶስ ተቃዋሚው ነው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁴ ነገር ግን ጴጥሮስ ከአሥራ አንዱ ጋር ቆመ፥ ድምፁንም ከፍ አድርጎ እንዲህ ሲል ተናገራቸው፦ አይሁድ በኢየሩሳሌምም የምትኖሩ ሁላችሁ፥ ይህ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን፥ ቃሎቼንም አድምጡ።
¹⁵ ለእናንተ እንደ መሰላችሁ እነዚህ የሰከሩ አይደሉም፥ ከቀኑ ሦስተኛ ሰዓት ነውና፤
¹⁶ ነገር ግን ይህ በነቢዩ በኢዩኤል የተባለው ነው።
¹⁷ እግዚአብሔር ይላል፦ በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፥ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ፥ ሽማግሌዎቻችሁም ሕልም ያልማሉ፤
¹⁸ ደግሞም በዚያች ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ ትንቢትም ይናገራሉ።
¹⁹ ድንቆችን በላይ በሰማይ፥ ምልክቶችንም በታች በምድር እሰጣለሁ፤ ደምም እሳትም የጢስ ጭጋግም ይሆናል፤
²⁰ ታላቅ የሆነ የተሰማም የጌታ ቀን ሳይመጣ ፀሐይ ወደ ጨለማ ጨረቃም ወደ ደም ይለወጣሉ።
²¹ የጌታን ስም የሚጠራም ሁሉ ይድናል።
²² የእስራኤል ሰዎች ሆይ፥ ይህን ቃል ስሙ፤ ራሳችሁ እንደምታውቁ፥ የናዝሬቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር በመካከላችሁ በእርሱ በኩል ባደረገው ተአምራትና በድንቆች በምልክቶችም ከእግዚአብሔር ዘንድ ለእናንተ የተገለጠ ሰው ነበረ፤
²³ እርሱንም በእግዚአብሔር በተወሰነው አሳቡና በቀደመው እውቀቱ ተሰጥቶ በዓመፀኞች እጅ ሰቅላችሁ ገደላችሁት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_21_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇🌹

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወገሠጸ ነገሥተ በእንቲአሆሙ። ኢትግሥሡ መሲሐንየ። ወኢታኅሥሙ ዲበ ነቢያትየ። መዝ.104÷14-15

#ትርጉም፦ “የቀባኋቸውን አትዳስሱ፥ በነቢያቴም ክፉ አታድርጉ ብሎ፥ ሰው ግፍ ያደርግባቸው ዘንድ አልፈቀደም፥ ስለ እነርሱም ነገሥታትን ገሠጸ።” መዝ.104÷14-15
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጥቅምት_21_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዮሐንስ 11
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³⁸ ጌታችን ኢየሱስም በራሱ አዝኖ ወደ መቃብሩ መጣ፤ እርሱም ዋሻ ነበረ፤ ድንጋይም ተገጥሞበት ነበር።
³⁹ ጌታችን ኢየሱስ፦ ድንጋዩን አንሡ አለ። የሞተውም እኅት ማርታ፦ ጌታ ሆይ፥ ከሞተ አራት ቀን ሆኖታልና አሁን ይሸታል አለችው።
⁴⁰ ጌታችን ኢየሱስ፦ ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር እንድታዪ አልነገርሁሽምን? አላት።
⁴¹ ድንጋዩንም አነሡት፦ ጌታችን ኢየሱስም ዓይኖቹን ወደ ላይ አንሥቶ፦ አባት ሆይ፥ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ።
⁴² ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ አለ።
⁴³ ይህንም ብሎ በታላቅ ድምፅ፦ አልዓዛር ሆይ፥ ወደ ውጭ ና ብሎ ጮኸ።
⁴⁴ የሞተውም እጆቹና እግሮቹ በመግነዝ እንደ ተገነዙ ወጣ፤ ፊቱም በጨርቅ እንደ ተጠመጠመ ነበር። ጌታችን ኢየሱስም፦ ፍቱትና ይሂድ ተዉት አላቸው።
⁴⁵ ስለዚህ ወደ ማርያም ከመጡት፥ ጌታችን ኢየሱስም ያደረገውን ካዩት ከአይሁድ ብዙዎች በእርሱ አመኑ፤
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 🌹
  የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን #የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የ #እመቤታችን የተዓምር በዓል፣ የነብዩ ቅዱስ ኢዩኤል የዕረፍት በዓል፣ የቅዱስ አልዓዛር የሥጋው ፍልሰት፣ የቅዱስ አላኒቆስ የዕረፍት በዓል እና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነቢዩ_ኢዩኤል

በስመ #አብ_ወወልድ_ወመንፈስ_ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

#ኢዩኤል” ማለት “ #እግዚአብሔር አምላክ ነው” ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱሳችን እንደምንመለከተውም “ኢዩኤል” የሚለው ስም በዕብራውያን የተለመደ መኾኑ ነው /፩ኛ ሳሙ.፰፡፪፣ ፩ኛ ዜና ፬፡፴፭፣ ፪ኛ ዜና ፳፱፡፲፪፣ ዕዝራ ፲፡፵፫/፡፡
አባቱ ባቱአል እናቱም መርሱላ ይባላሉ፡፡ የመጽሐፉ የአንድምታ ትርጓሜ መቅድም እንደሚናገረው ነገዱ ከነገደ ሮቤል ወገን ነው፡፡ ሌሎች ሊቃውንት ግን ኢዩኤል ከነገደ ይሁዳ ወገን እንደኾነ ይናገራሉ፡፡ ለዚኽ አባባላቸው እንደ ማስረጃ የሚያስቀምጡትም አንደኛ ኢዩኤል ይኖር የነበረው በኢየሩሳሌም መኾኑ፤ ኹለተኛ በመጽሐፉ ስለ ካህናት ማንሣቱ /፩፡፲፫/፤ ሦስተኛ ስለ ቤተ መቅደስ መናገሩ /፩፡፱/፣ እና ሌላም ሌላም በማለት ነው፡፡

በብዙ ሊቃውንት ዘንድ ነቢዩ ኢዩኤል የነበረበት ዘመን ላይ ልዩነት አለ፡፡ አንዳንዶቹ ከምርኮ በፊት ነበረ ሲሉ ሌሎች ደግሞ “አይደለም ከምርኮ በኋላ የነበረ ነው” ይላሉ፡፡ ኹለቱንም ወገኖች የሚያቀርቡትን ማስረጃ እናስቀምጥና አንባብያን የየትኞቹ አሳማኝ እንደኾነ ማየት ይችላሉ፡፡ አስቀድመንም “ከምርኮ በኋላ ነበረ” የሚሉትን እንመልከት፡፡ እነዚኽ ሊቃውንት ነቢዩ ኢዩኤል ከምርኮ በኋላ ነበረ ለማለት ያነሣሣቸው፡-
1.ነቢዩ ኢዩኤል በዘመኑ ስለ ነበረው ንጉሥ ሳይናገር ይልቁንም ስለ ካህናትና ስለ ሽማግሌዎች መናገሩ በእስራኤልና በይሁዳ ከምርኮ ከተመለሱ በኋላ ንጉሥ ስላልነበራቸው ነው፡፡

2.ነቢዩ ኢዩኤል ስለ ሰሜናዊው ግዛት ማለትም ስለ እስራኤል አለመናገሩና ስለ ይሁዳ ብቻ መናገሩ ዘመኑ ከምርኮ በኋላ መኾኑ ያመለክታል፡፡

3.ነቢዩ ኢዩኤል ከኢየሩሳሌም ውጪ በሰማርያ ስለ ነበሩ የአምልኮ ዐፀዶች ምንም አላለም፡፡ ስለ አምልኮተ ጣዖትና ስለ በኣልም ምንም አላለም፡፡ እነዚኽ ደግሞ ገንነው ይታዩ የነበረው ከምርኮ በፊትና በምርኮው ጊዜ እንጂ ከምርኮ በኋላ አይደለም፡፡

4.ነቢዩ ካህናቱን፡- “የ #እግዚአብሔር አገልጋዮች” ብሎ ጠርቷቸዋል /፩፡፲፫/፡፡ ይኽ ዓይነቱ አጠራር ደግሞ ከምርኮ በኋላ ባለው ጊዜ በጣም በተደጋጋሚ ይዘወተር የነበረ አባባል ነው፡፡

አኹን ደግሞ “ከምርኮ በፊት የነበረ ነው” የሚሉ ሊቃውንት ለትምህርታቸው እንደ ማስረጃ የሚያቀርቡትን እንመልከት፡-
1.ነቢዩ በጊዜው የነበረውን ንጉሥ ማን እንደኾነ አለመጥቀሱ ንጉሡ ገና ሕፃን ስለ ነበረ ሊኾን ይችላል፡፡ ይኸውም ኢዮአስ መንገሥ የዠመረው በሰባት ዓመቱ እንደነበረ ማለት ነው /፪ኛ ዜና.፳፬፡፩/፡፡ ሕፃን ከኾነ ደግሞ የሚነገረው ነገር ማመዛዘን ስለማይችል፡- “እገሌ ንጉሥ ሳለ እንዲኽ ያለ ትንቢት ተናገርኩ” ቢል ተቀባይነት የለውም፡፡ ወይም ደግሞ ነቢዩ የሚፈልገው የሕዝቡን የ #ንስሐ ሕይወት እንጂ የፖለቲካ ጉዳይ ስላልኾነ ነው፡፡

2. ነቢዩ ስለ አምልኮተ ጣዖት፣ ወይም ስለ በዓል አለመናገሩ የትንቢት መጽሐፉን ከምርኮ በኋላ መጻፉን አያመለክትም፡፡ ይልቁንም የስብከቱ መንገድ አንዱን አቅጣጫ ማለትም ስለ በዓልና ስለ አምልኮተ ጣዖት ሳይናገር #እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና ማምለክ እንዳለባቸው መንገርን ስለ መረጠ ነው፡፡

3.ብዙ ነቢያት ለምሳሌ እነ ቅዱሳን ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ፣ ሕዝቅኤል እና አሞጽ ከትንቢተ ኢዩኤል መጽሐፍ ጠቅሰው ተናግረዋል፡፡ ስለዚኽ ነቢዩ ከእነዚኽ በፊት ነበረ ማለት ነው፡፡

4.ነቢዩ ኢዩኤል ምርኮ እንደሚኾን ተናገረ እንጂ እንደኾነ አልተናገረም /ኢዩ.፫፡፪-፫/፡፡ ይኽም ከምርኮ በፊት እንደ ነበረ ያስረዳል፡፡

5.ነቢዩ ግብጽ የይሁዳ ባላንጣ እንደኾነች ተናግሯል /፫፡፲፱/፡፡ ይኽም ከምርኮ በፊት እንጂ ከምርኮ በኋላ ሊኾን አይችልም፡፡ ከዚኽም በተጨማሪ ከምርኮ በፊት ስለነበሩ የይሁዳ ጠላቶች ማለትም ስለ ጢሮስ፣ ስለ ሲዶና፣ ስለ ፍልስጥኤማውያን /፫፡፬/፣ ስለ ኤዶምያስ /፫፡፲፱/ መናገሩ ነቢዩ ከምርኮ በፊት እንደነበረ ያሳያል፡፡

6. ነቢዩ ስለ ሰሜናዊው መንግሥት ማለትም ስለ እስራኤል አለመናገሩና ጠቅለል አድርጐ ስለ እስራኤል መናገሩ አንደኛ ኹለቱም ሕዝቦች አንድ በመኾናቸው /፪፡፳፯፣ ፫፡፲፮/፤ ኹለተኛው የነቢዩ አገልግሎት በይሁዳ ስለነበር፤ ሦስተኛውና ዋናው ደግሞ ነቢዩ በትንቢት መነጽር በአዲሲቱ እስራኤል (በቤተ ክርስቲያን) መለያየት እንደሌለና ኹሉም አንድ እንደሚኾኑ ሲናገር ነው፡፡

🌹 #ትንቢተ_ኢዩኤል 🌹

ምንም እንኳን ነቢዩ ኢዩኤል የይሁዳን ከተማ የሚወርራት አስፈሪውን የአንበጣ መንጋ ድምፅ ቢሰማም፤ ምንም እንኳን የአንበጦቹ መንጋ ሰማዩን ሲከድነው፣ ፀሐይቱ ስትጨልም፣ ኹሉም ጭጋጋም ኾኖ ቢመለከትም፤ ምንም እንኳን ዛፉ ኹሉ ደርቆ ምድሪቱ ምድረ በዳ ስትኾን ቢያይም ከዚያ ጀርባ የነበረችይቱን የ #እግዚአብሔር ጣትም ያይ ነበር፡፡ የ #እግዚአብሔር እጅ ይኽን ኹሉ እንዳደረገችና ሕዝቡን ለመቈንጠጥ ጥበብ ሰማያዊ መኾኑን ያስተውል ነበር፡፡

ነቢዩ ኢዩኤል፥ ሕዝቡ የአንበጦቹን ቋንቋ አላደምጥ ሲል የድርቁን ተግሳጽ አልሰማ ሲል በምርኮ እንደሚኼድ ቢመለከትም ይኽም የ #እግዚአብሔር ፈቃድ እንደነበረ በትንቢት አጉሊ መነጽር አይቷል፡፡ ደጋግሞ “የጨለማና የጭጋግ ቀን፣ የ #እግዚአብሔር ቀን” እያለ የጠራትም ይኽቺው የሕዝቡ የምርኮ ቀን ናት /፪፡፩-፫/፡፡

ምንም እንዲኽ ቢኾንም ግን #እግዚአብሔር ሕዝቡን ያለ አንዳች ተስፋ እንዳልተዋቸውም ጨምሮ ተናግሯል፤ መንፈሱን በሥጋ ለባሽ ኹሉ ላይ እንደሚያፈስና የሰው ልጆችን በሙሉ ለታላቂቱ የ #ጌታ ቀን እንደሚያዘጋጃቸው አብሮ ተናገረ እንጂ፡፡ በዚኽም #እግዚአብሔር ራሱ ረዳት እንደሚኾናቸውና ለክፉዎቹ የጨለማ ቀን እንደሚኾንባቸው ለመልካሞቹ ግን የብርሃን ቀን እንደሚኾንላቸው ተናገረ፡፡

መጽሐፉ በአጠቃላይ #እግዚአብሔር በሰው ልጆች ላይ ያለውን ዕቅድ የሚያስረዳ ነው፡፡ #እግዚአብሔር ሕዝቡን በተለያየ ቋንቋ (በአንበጦቹ፣ በድርቁ፣ በምርኮው …) ሲያናግራቸው አንዳች ነገር ከእነርሱ አልሰወረባቸውም፤ የክብሩ ተካፋይ ይኾኑ ዘንድ #መንፈስ_ቅዱስ ስንኳ ከመስጠት አልከለከላቸውም፡፡

ይኽ መጽሐፍ #መንፈስ_ቅዱስ በሥጋ ለባሽ ኹሉ ላይ እንደሚፈስ የሚያስረዳ መጽሐፍ ነው፡፡ ሌሎች ነቢያት ክብር ይግባውና #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በድንግና ተፀንሶ በድንግልና ተወልዶ የዓለምን ኃጢአት እንደሚያስወግድ ሲናገሩ ትንቢተ ኢዩኤል ግን ስለ ዓለም ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ስለሚወቅስ ስለ #መንፈስ_ቅዱስ አብዝቶ የሚናገር መጽሐፍ ነው /ዮሐ.፲፮፡፰/፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል አብዝቶ የሚናገረው #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በደሙ የዋጃትን ቤተ ክርስቲያን በጽድቅና በቅድስና እንድትቀጥል ስለሚያድገው አጽናኝ #መንፈስ_ቅዱስ ነው፡፡ አብዝቶ የሚናገረው በረኻ የኾነውን የሰውን ልቡና ምድረ ገነት ወደመኾን ስለሚለውጠው #መንፈስ_ቅዱስ ነው፡፡

ነቢዩ የአንበጣ መንጋ ዘሩን፣ ዛፉን፣ ቅጠሉን ጨርሶት እርሻውም ኹሉ ደርቆ ምድረበዳ እንደኾነ መናገሩ ኃጢአት የተባለ አንበጣ “የ #እግዚአብሔር እርሻ፣ ወይን፣ በለስ፣ ሮማን፣ ተምር፣ እንኮይ፣ የምድር ዛፍ” የተባለውን የሰውን ልጅ ክብሩን እንዳሳጣው ሲናገር ነው /፩፡፲፪/፡፡ የኃጢአት እሳት፥ እርሻ የተባለውን ሰው እንደበላ (እንዳቃጠለ) አስቀድሞ መናገሩ ይኽን እርሻ ዳግም ወደ ገነት የሚመልስ ሌላ እሳት (ይኸውም #መንፈስ_ቅዱስ ነው) እንደሚያስፈልግ ይናገር ነበር፡፡
ሊቃውንት እንደሚናገሩት፡- “ምንም እንኳን ነቢዩ ኢዩኤል ደጋግሞ የ #ጌታ ቀን፣ የ #እግዚአብሔር ቀን እያለ ቢናገርም ይኽን መቼ እንደተናገረው፣ በእርሱ ዘመን የነበሩ ነገሥታትም እነማን እንደኾኑ አለመጥቀሱ መጽሐፉ ለትውልድ ኹሉ መጻፉን የሚያመለክት ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ የ #ጌታ ቀን ብለን የምናውቃት የምጽአት ቀን መቼ እንደኾነች የሰው ልጅ በሙሉ እንዳያውቃትና ይልቁንም ዘወትር ዝግጁ ኾኖ እንዲኖር ከመሻት አንጻር ነው” ይላሉ፡፡

ምንም እንኳን እያንዳንዱ የ #እግዚአብሔር ነቢይ ሕዝቡ ከኃጢአት እንዲመለስ ለማድረግ #እግዚአብሔር በሕዝቡ ላይ ሊያመጣ ያሰበውን ቁጣ ቢናገሩም በአጠቃላይ ግን የመሲሑን የማዳን ሥራ፣ የዳዊት ልጅ፣ መንፈሳዊው ንጉሥ፣ አገራትን ኹሉ ወደ አባቱ ዕቅፍ የሚያመጣውን መሲሕ በተዋሕዶ ከብሮ እንደሚመጣ በመናገር ነው፡፡ ሕዝቡ ከሚደርስባቸው ጊዜአዊ ችግር ተሸግረው ይኽን የመሲሑ ዘመን እንዲመለከቱ ያደረጉበት መንገድ ግን የተለያየ ነው፡፡ ቅዱሳን ኢሳይያስ፣ አሞጽና ሚክያስ #ንስሐ ላይ ትኩረት ያደርጋሉ፤ ቅዱሳን ዕዝራና ነህምያ የ #እግዚአብሔርን ቤተ መቅደስና የኢየሩሳሌምን አጥር በማነፅ እንዲመለሱ ያደርጋሉ፤ ቅዱሳን ሕዝቅኤልና ኤርምያስ ደግሞ አፍአዊ በኾነ መንገድ ሳይኾን ልቡናቸውን ለውጠው ወደ #እግዚአብሔር መምጣት እንዳለባቸው ይናገራሉ፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል ግን አፍአዊውን የኢየሩሳሌም ቅጥር፣ የቤተ መቅደሱን መታነፅ፣ የካህናቱን አኳኃን ቢመለከትም ስለ ውሳጣዊቷ ኢየሩሳሌም፣ ስለ ምስጢራዊው ቤተ መቅደስ፣ ስለ ልቡናም ጨምሮ ይናገራል፡፡ ነቢዩ፥ የ #እግዚአብሔር ሕዝብ ግላዊ በኾነ እይታ እንዲመለከት አይጋብዝም፤ የቤተ ክርስቲያን ሕዋስ እንደመኾኑ “እኛ” በሚል መንፈስ ይናገራል እንጂ፡፡ በደሉን የሠሩት በአንድ ላይ እንደመኾናቸው መመለስም ያለባቸው በአንድ ላይ መኾን እንዳለባቸው ይናገራል፡፡ አንዱ አንዱን እንዲረዳ ያበረታታል፡፡

ነቢዩ ኢዩኤል “የኦሪት ነቢይ” እየተባለ ይጠራል፤ ይኸውም ከአምስቱ የሙሴ መጻሕፍት ፳፭ ጊዜ ጠቅሶ ስለሚናገር ነው፡፡ ዳግመኛም ስለ #መንፈስ_ቅዱስ አብዝቶ ስለሚናገር“የ #ጰንጤ_ቆስጤ ነቢይ” ይባላል፡፡

🌹 #መጽሐፉን እንደሚከተለው መክፈል እንችላለን፡-

1. የአንበጣ መንጋ አገሩን እንደወረረ /ምዕ. ፩/፤
2. ጠላት መጥቶ እንደሚወራቸው /ምዕ. ፪፡፩-፳፯/፤
3. ርደተ #መንፈስ_ቅዱስ /ምዕ. ፪፡፳፰-፴፪/፤
4. ታላቂቱ የ #እግዚአብሔር ቀን /ምዕ. ፫/።

#ተመስጦ
ቸርና #ቅዱስ_እግዚአብሔር_ሆይ! ነቢዩ ኢዩኤል እንደተናገረ ኃጢአት እንደ አንበጣ መንጋ ኹለንተናችን ወረረው፡፡ የመንፈስ ፍሬ እንዳናፈራ የኃጢአት ኩብኩባ ልቡናችንን በላው፡፡ ገነት ልቡናችንንም ምድረበዳ አደረገው፡፡ የኃጢአት መንጋ መቅደስኽ ልቡናችንን አቆሸሸው፡፡ ደስታ ከእኛ ዘንድ ራቀ፡፡ የንጉሥ ልጆች ብንኾንም በገዛ ፈቃዳችን “ገብሩ ለዲያብሎስ፣ አመቱ ለዲያብሎስ” ተብለን ወደ ባርነት ኼድን፡፡ መዓዛ መለኮትኽ ከእኛ ዘንድ ራቀ፡፡ በረከትኽን አርቀን ፍርድን በላያችን ላይ ጨመርን፡፡ አንተም ከገነት እንድንወጣ አደረግከን፡፡
ቅዱስና ርኅሩኅ አባት ሆይ! ከገነት እንድንወጣ ማድረግኽ ግን የፍቅርኽ መገለጫ ነበር፡፡ ከገነት ስታወጣን ዕድፈታችንን አስወግደኽ ዳግም ወደ ጥንተ ተፈጥሮአችን ለመመለስ ነበርና ከፍቅርኽ የተነሣ ወጣን፡፡ ወዮ! ከቁንጥቻኽ ጋር አብሮ የሚታየው ፍቅርኽ እንደምን ይረቃል? እንደምን ይመጥቃል? ከቁንጥጫኽ ጀርባ ያለው የፍቅር እጅኽን ያየ ሰውም ንዑድ ክቡር ነው፡፡
#ቅዱስ_አባት_ሆይ! ስንወጣም እንደወጡ ይቅሩ አላልከንም፡፡ እንደቃልኽ ፈለግከን እንጂ፡፡ እንደ ፍቅርኽ በትከሻኽ ተሸከምከን እንጂ፡፡ ፍርዳችንን ተሸክመኽ ዳግም ልጆችኽ አደረግከን እንጂ፡፡ በቈሰለው ማንነታችን፣ በመረቀዘው ልቡናችን ላይ ዘይትን አፈሰስክልን፡፡ ቅድስናችን አንተው ራስኽ ኾንከን፡፡ ይኽም ሳይበቃ ቅድስናችንን እንዳናቆሽሽ መጽንዒ #መንፈስ_ቅዱስን ላክልን፡፡ በረኻው ልቡናችንንም ገነት ወደ መኾን መለስክልን፡፡
እኛ ግን የተደረገልንን ረስተን የኃጢአት አንበጣ የኃጢአት ኩብኩባና ደጎብያ እየጠራን እንገኛለን፡፡ #ቅዱስ_አባት_ሆይ! አንተ ግን አትተወን፡፡ #ቅዱስ_መንፈስኽን አትውሰድብን፡፡ ከምርኮ መልሰን፡፡ ደካሞች ነንና እርዳን፡፡ መሻት እንጂ ብርታቱ የለንምና ደግፈን፡፡ ለታላቂቱ ቀን የተዘጋጀን አድርገን፡፡ አሜን!!!

ዋቢ ድርሳናት፡- ➣የትንቢተ ኢዩኤል አንድምታ፤
➣የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት
🌹 "በስመ #አብ_ወወልድ_ወመንፈስ_ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹

#ጥቅምት ፳፩ (21) ቀን። እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ መሰቀልህን በቅዱሳት መጻሕፍት ሰማሁ ይኽን በዐይኔ አሳየኝ በማለት #መድኃኔዓለምን_ለጠየቁት_እሱም ለገለጸላቸው፤ የንጉሡን መልዕክተኞች ከንጉሡ ቤት እንገናኝ በማለት መልዕክተኞቹ ዘጠኝ ቀን ተጉዘው ሲደርሱ እሳቸው ቀድመዋቸው ንጉሡ ቤት ለተገኙት #አቡነ_ዐሥራተ_ወልድ_ለዕረፍታቸው በዓል #እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።

                              
🌹 #አቡነ_ዐሥራተ_ወልድ፦ በዳሞት አውራጃ ልዩ ስሟ እነሴ በምትባል ቦታ በዐፄ ሠርጸ ድንግል ዘመነ መንግሥት በ1584 ዓ.ም ተወለዱ። አባታቸው ፃማ #ክርስቶስ እናታቸው ጽጌ #ማርያም ይባላሉ። ኹለቱም በሕገ #እግዚአብሔር ጽንተው የሚኖሩ በሃይማኖት በምግባር የተመሰገኑ በተጋድሎ በትሩፋት የታወቁ ክርስቲያኖች ነበሩ ነገር ግን ልጅ ስላልነበራቸው እንደ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ የተባረከ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ሁልጊዜ #እግዚአብሔርን በጸሎት ይጠይቁ ነበር አምላክን የወለደች ክብርት #እመቤታችንንም ይማጸኗት ነበር።

ኹለቱም #እግዚአብሔርን የሚፈሩ በምድራዊ ሀብትም የበለጸጉ ነበሩ፤ ለድኖችና ለምስኪኖች አብዝተው ይመጸውቱ ስለነበር ከጾማቸው በኋላ ያለ ድኖችና ምስኪኖች ብቻቸውን አይመገቡም ነበር። #እግዚአብሔርም ጸሎት ልመናቸውን ተቀብሎ የተባረከ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ወደደ። ከዕለታትም በአንደኛው ቀን የ #እግዚአብሔር ሰው ለጽጌ #ማርያም ታይቶ "ዝናው በአራቱ ማዕዘን ኹሉ የሚደርስ በሕይወተ ሥጋ እያለ የብዙ ሰዎችን ነፍስ በጸሎቱ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የሚያወጣ ወደ ሰማይም ወጥቶ የ #ሥላሴን ምሥጢር የሚያይ የተባረከ ልጅን ትወልጂ ዘንድ አለሽና ደስ ይበልሽ" በማለት ካበሠራት በኋላ አቡነ ዐሥራተ ወልድ ሰኔ ሃያ ቀን ተወለዱ።

ጻድቁም በተወለዱ በስምንተኛ ቀናቸው "ለ #አብ ምስጋና ይገባል ለ #ወልድ ምስጋና ይገባል ለ #መንፈስ_ቅዱስ ምስጋና ይገባል" ብለው ፈጣሪያቸውን አመስግነዋል። እስከ ዐሥራ ኹለት ዓመታቸውም ድረስ ውኃ በመቅዳት ዕንጨት በመስበር ወላጆቻቸውን ካገለገሉ በኋላ ወላጆቻቸው ወደ ታላቁ ጻድቅ ወደ አቡነ ተጠምቀ መድኅን ዘንድ ወስደው እንዲያስተምሩላቸው አደራ ብለው ሰጧቸው።

አቡነ ተጠምቀ መድኅንም ዐሥራተ ወልድን ተቀብለው የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ኹሉ አስተማሯቸው። በሚማሩበትም ጊዜ #መንፈስ_ቅዱስ በአፋቸው ያቀብላቸው ስለነበር አስቀድመው የተማሩ ይመስሉ ነበር። በሦስት ዓመትም ውስጥ መጻሕፍተ ብሉያትን መጻሕፍተ ሐዲሳትን መጻሕፍተ መነኰሳትን፣ አዋልድ መጻሕፍትንም ኹሉ ከነትርጓሜያቸው ከአቡነ ተጠምቀ መድኅን ተምረው #እግዚአብሔርም ከሐሰት መጻሕፍት ከሟርት ከጥንቆላ መጻሕፍት በቀር ያልገለጠላቸው የመጻሕፍት ምሥጢር የለም። የመላእክትንና የቅዱስ ያሬድንም ዜማ ገለጠላቸው።

ከዚኽም በኋላ አቡነ ዐሥራተ ወልድ ለመመንኰስ ወላጆቻቸውን አስፈቅደው ከመምህራን ጋር ወደ ታላቁ ገዳም ወደ ደብረ ዳሞ ሔደው በዚያም መነኰሳቱን እያገለገሉ ለ25 ዓመታት ያህል በተጋድሎ ከኖሩ በኋላ በዐፄ ፋሲል ዘመን መንግሥት በ40 ዓመታቸው በ1624 ዓም መንኰሱ። ከሊቀ ጳጳሱ ከአቡነ ሚካኤልም እጅ የቅስና ማዕረግ ተቀበሉ። ከዚኽም በኋላ ከመምህራቸው ከአቡነ ተጠምተ መድኅን ጋር ወደ ጋሾላና ጉሓን ገዳማት ሔደው ተጋድሏቸውን ጨምረው መጾም መጸለይን አበዙ። ወደ ተራራ ሔደው ዳዊት ሲያነቡ ያድራሉ፣ ምሥራቅም ዙረው አምስት መቶ ጊዜ ይሰግዳሉ፤ ወደ ምዕራብም ዙረው አምስት መቶ ጊዜ ይሰግዳሉ፤ ወደ ሰሜንም ዙረው አምስት መቶ ጊዜ ይሰግዳሉ ወደ ደቡብም ዙረው እምስት መቶ ጊዜ ይሰግዳሉ፤ እንዲህም እያደረጉ በየዕለቱ ኹለት ሺህ ይሰግዱ ነበር። ላባቸው እንደ ውኃ ፈስሶ ምድርን እስኪያርስ ድረስ ይሰግዳሉ፤ የቆሙበትም ምድር እንደ ጉድጓድ ይጎደጉዳል። እንደዚህ ባለ ታላቅ ተጋድሎ ጸንተው ብዙ ዘመን ኖሩ። የ #ጌታችንንም ዐርባ ጾም ምንም ሳይቀምሱ ዐርባውን ቀን ይጾሙ ነበር።

ከዚኸም በኋላ አቡነ ዐሥራት ወልድ ጃባ በሚባለው ቦታ ዐሥራ አንድ ዓመት በተጋድሎ ኖሩ። አባታችን ያከብሯት የነበረች ቅዱስ ሉቃስ የሣላት የክብርት #እመቤታችን ሥዕል በዚያ ነበረችና እርሷም ድንቅ ድንቅ ተኣምራትን ታደርግላቸው ነበር። ጃባ በምትባል ቦታም ዘወትር ታነጋግራቸው ነበር። በአንደኛውም ሌሊት ተኝተው ሳሉ አምላክን በድንግልና የወለደች ክብርት #እመቤታችን ተገልጣላቸው "ልጄ ወዳጅ ዐሥራተ ወልድ ሆይ! በጸሎትና በልመናህ የጃባ ሰዎች ኹሉ ይድናሉ፣ በቃልህ #ክርስቶስን አምነው በእጅህ #ቅዱስ_ሥጋውንና #ክቡር_ደሙን ይቀበላሉ" አለቻቸው።

ከዚኽም በኋላ የታዘዘ የ #እግዚአብሔር መልአክ ለኹለቱም ቅዱሳን ተገልጦላቸው አቡነ ተጠምቀ መድኅንን ወደ ጋዝጌ እና ወደ መተከል ሔደው የከበረች ወንጌልን እንዲያስተምሩ ሲያዛቸው አቡነ ዐሥራተ ወልድን ደግሞ ወደ ጫራ ምድር ሔደው በዚያ ወንጌልን ይሰብኩ ዘንድ አዘዛቸው። ኹለቱም ቅዱሳን እርስ በርሳቸው በመንፈሳዊ ሰላምታ እጅ ተነሣሥተው ለሐዋርያዊ አገልግሎት ተለያይተው ወደታዘዙባቸው ቦታዎች ሔዱ። አባታችን ዐሥራተ ወልድም እየጸለዩ ስምንት ዓመት ከስድስት ወር በርበር በምትባል በረሓ ውስጥ ሳሉ በአራቱም ማዕዝናት እየተዘዋወሩ በምሥራቅ አንድ ሽህ በምዕራብ አንድ ሺህ በሰሜን አንድ ሺህ በደቡብ አንድ ሺህ ጊዜ ይስግዱ ጀመር የክብር ባለቤት #ጌታችን_አምላካችን_ኢየሱስ_ክርስቶስም በዚህ ጊዜ ተገልጦላቸው "ወዳጀ ዐሥራተ ወልድ ሆይ! ለምን ሥጋህን እንደዚህ አደከምህ" አላቸው አባታችንም " #ጌታ ሆይ! ኃይላቸውን በስግደት ቀንና ሌሊት በመትጋት የሚያደክሙ በመንግሥትህ አይደሰቱምን በዓለም የደከመ ለዘለዓለም ይድናል ጻድቃን ዳግመኛም በብዙ ድካምና መከራ ወደ #እግዚአብሔር መንግሥት እንገባ ዘንድ ይገባናል" እንዳለ በማለት መለሱ። #ጌታችን_መድኀኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ "ድካምህ በከንቱ አትቀርም በሰማያውያን መላእክት በተባረኩ ጻድቃን ድል በነሱ ሰማዕታት ንጹሐን በሚሆኑ ደናግል በፍጹማን መነኰሳት ፊት የድካምህን ዋጋ እሰጥሃለሁ። እንግዲህ ከዛሬ ጀምረህ ወደ አዘዝኩህ ቦታ ሒድ፤ "መንግሥተ ሰማያትም ቀርባለች" እያልህ የመንግሥትን ወንጌል አስተምር፣ ኃይሌ ከአንተ ጋር ይኖራልና" ብሎ አዘዛቸው።

#ጌታችን ይህን ሲነግራቸው አውሎ ነፋስ መጥቶ ጉርብ ወደ ምትባለው ዋሻ ወስዶ አደረሳቸው። በሥራ የሚኖሩ የሀገሩ ሰዎችም የአባታችን ዐሥራተ ወልድን መምጣት ሰምተው ተቆጥተው በአባታችን ላይ በጠላትነት ተነሡባቸው፣ ጋሻቸውንና ጦራቸውን ይዘው የመጡ ቢሆንም አባታችን ግን የከበረች የ #ክርስቶስን ወንጌል አስተምረው አሳምነው አጠመቋቸው። የጫራንም ሕዝብ አምስት ዓመት ካስተማሯቸው በኋላ ዳግመኛ የሻሽናን ሕዝብ ያስተምሯቸው ዘንድ የ #እግዚአብሔር መልአክ እየመራው ሻሽና አደረሳቸው። አባታችን በዚያም የሀገሩን ሕዝብ አስተምረው አጠመቁ።
የጎንደር ንጉሥ ጻድቁ ዮሐንስ የአባታችን ዐሥራተ ወልድን ቅድስናና ገድል በሰማ ጊዜ ወደ እርሱ ያመጧቸው ዘንድ መልእክተኞችን ላከ፤ መልእክተኞችም አባታችንን በሻሽና አገኟቸው፤ አባታችን ግን መልእክተኞቹን "ልጆቼ እኔ ኃጢአተኛ ስሆን ከጎንደር እስከ ሻሽና ንጉሡ ምን ብሎ ላካችሁ?" አሏቸው። ይኸንንም ተናግረው የንጉሥን ጭፍራ "ወደ እናንተ እስክመለስ ድረስ ከዚኸ ጠብቁ" ብለው ወደ ንጉሡ ዘንድ ከመሔዳቸው በፊት ወደ ጸሎት ቤት ገብተው ከዳዊት መዝሙር ጸለዩ። ጸሎታቸውንም ከፈጸሙ በኋላ አባታችን ወደ እነርሱ ተመልሰው "እኔ ሽማግሌ ሰው ነኝ ወደ ጎንደር ለመሔድ አልችልም" አሏቸው። እነርሱም "አባታችን ሆይ! አንተ ከእኛ ጋር ካልሔድህ ተመልሰን አንሔድም" አሉ። አባታችንም እጅግ አዝነው "ልጆቼ ሒዱ እኛ እርሰ በእርሳችን በንጉሡ ቤት እንገናኘለን አሏቸውና ተመልስው ሔዱ ተመልስው ከሔዱ በኋላ ወደ ንጉሡ ቤት ቢደርሱ አባታችንን ከንጉሡ ጋር ተቀምጠው አገኟቸው።

የንጉሡ መልእክተኞችም ለንጉሡ "እኛ ከሻሽና ከተነሣን እስከዚህ ዘጠኝ ቀናችን ነው ይኽ አባት የሚያስደንቅ ተአምር እያደረገ በየት አለፈን?" ብለው እጅግ ተገረሙ። ንጉሡም ይኽን ድንቅ ተኣምር በስማ ጊዜ ከአባታችን እግር ሥር ሰገደ አቡነ ዐሥራተ ወልድንም "አባቴ ሆይ አስተምረህ ላሳመንኽውና ለአጠመቅኽው ሕዝብ ታቦትን ወስደህ ቤተክርስቲያን ሥራ ከታቦታትም የወደዱኻውን ምረጥ"። በማለት ጠየቃቸው። ብፁዕ አባታችን ዐሥራተ ወልድም "በጣም የምወዳት እንደ ምግብ የምመገባት እንደ መጠጥ የምጠጣት እንደ ልብስ የምለብሳት፣ እንደ ምርጉዝ የምደገፋት በፍቅሯ የምረካባት የ #ኪዳነ_ምሕረት ታቦት ናትና እርሷን እወዳታለሁ" ብለው መረጡ፤ ንጉሡም ቃላቸውን ሰምቶ ታላቅ ደስታ ተደሰተ ፈቀደላቸውም።

ከዚኽም በኋላ አቡነ ዐሥራተ ወልድ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው በዚያ " #ጌታየ ሆይ መሰቀልህን በቅዱሳት መጻሕፍት ሰማሁ ይኽን በዐይኔ አሳየኝ" እያሉ አንድ ዓመት ቆመው ጸለዩ። የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስም ለአባታችን ተገለጠላቸውና መጀመሪያ አይሁድ እንዴት እንደሰቀሉት የእሾኽ አክሊልን እንደአቀዳጁት፣ ጎኑን በጦር እንደተወጋ አሳያቸው። አቡነ ዐሥራተ ወልድም የ #ጌታችንን ስቅለት በተመለከቱ ጊዜ እጅግ ደንግጠው ወደቁ።

በዚያን ጊዜም #ጌታችን ወደ እርሳቸው መጥቶ "ልታይ የማትችለውን ዕለተ ዐርብ ለምን ለመንከኝ? እንግዲህ ተነሣና ወደ ሀገርህ ተመለስ የሰበሰብሃቸው መንጋዎችህ አንተን በማጣታቸው ተበትነዋልና" አላቸው። ከዚኽም በኋላ #ጌታችን ታላቅ የምሕረት ቃልኪዳን ገብቶላቸው በክብር ዐረገ። አባታችን ዐሥራተ ወልድም ከገዳማቸው ወጥተው ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው አንድ ዓመት ከቆዩ በኋላ በትንሣኤ ዕለት #ቅዱስ_ሥጋውንና #ክቡር_ደሙን ተቀብለው በ #መንፈስ_ቅዱስ ኃይል ተመስጠው ካህናት ጸሎተ ቅዳሴውን ሳይጨርሱ ገዳማቸው ዙርዙር ኪዳነ ምሕረት ደረሱ።

ከዚኽም በኋላ አባታችን ጉርብ በምትባል ዋሻ ውስጥ በአድያም ሰገድ ኢያሱ ዘመን ቤተ ክርስቲያንን ሠርቶላቸው መቶ ዐሥር ዓመት ከኖሩና #ጌታችንም ታላቅ የምሕረት ቃልኪዳን ከገባላቸው በኋላ የጥቅምት ወር በባተ በሃያ አንድ ቀን ከዚኽ ዓለም ድካም በሰላም ዐርፈዋል። ከአባታችን ከአቡነ ዐሥራተ ወልድ #እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከት ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!።
2025/10/31 07:28:47
Back to Top
HTML Embed Code: