tgoop.com/amennnnnnnnnnnnnnnnnnnn/7748
Last Update:
በጀር #ሥላሴ የሚገኘው ታሪካዊ ታላቅ ተራራ በልበሊት ኢየሱስን ግራኝ አሕመድ ሲያቃጥል ሁለት በወርቅ የታነጹ አብያተ ክርስቲያናት በፍቃደ #እግዚአብሔር እንደሰወረ አባቶች ይናገራሉ። ይኸም ጥንታዊና ታሪካዊ ተራራ አሁንም በቦታው የሚገኝ ሲሆን በዋሻው ውስጥ የክብር ባለቤት #ጌታችን በስደቱ ወራት ከእናቱ ድንግል #ማርያም፣ ከዮሴፍና ከሰለሜ ጋር ለጥቂት ጊዜ የተቀመጠበት ሲሆን አቡነ ዜና ማርቆስና አቡነ ተክለ ሃይማኖትም በምነና የተጋደሉበት ታላቅ ዋሻ ነው። ዋሻው እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ውስጥ ለውስጥ የሚያስኬድ ሲሆን በውስጡ ከ40 በላይ አብያተ ክርስቲያናት እንደተሰወሩበት አባቶች ይናገራሉ።
በግራኝ አሕመድ ወረራ ወቅት የግራኝ ሠራዊት አብያተ ክርስቲያናቱን እናጠፋለን ብለው ሲመጡ በተኣምራት ሰምጠው እንደጠፉ አባቶች ያስረዳሉ። አዛዦቹንም በዋሻ ውስጥ የሚገኙት ወፍ የሚያህሉ ተርቦች ነድፈው ጨርሰዋቸዋል። እነዚያ ተርቦች አሁንም ድረስ በገዳሙ ውስጥ ያልተፈቀደ ነገር ሲደረግ በመናደፍና በመከልከል ዋሻውን የሚጠብቁ ሲሆኑ አንዱ ተርብ ከነደፈ ሕይወት ሊያጠፋ እንደሚችል የገዳሙ አባቶች ይናገራሉ። ከዚኸም በላይ ዋሻው በነብርም ይጠበቃል።
ገዳሙ ባለብዙ ቃልኪዳን ሲሆን ብዙ ስውራን አበው ዛሬም የሚኖሩበት ትንቢታቸው የማይነጥብ ብዙ ግሁሳን የከተሙበት ነው። ስውራኑ አበው ዛሬም #እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው ይገለጣሉ። ደገኞቹ የኢትዮጵያ ቀደምት ነገሥታት የገዳሙን ክብር በመረዳት ቦታው ድረስ በመሔድ በረከት ይቀበሉ ነበር። ዳግማዊ ምኒሊክ ለጀር #ሥላሴ ገዳምና ለገዳማውያኑ አለኝታ ስለነበሩ በገዳሙ የታሪክ መዝገብ ስማቸው ዘወትር ይነሳል። ግርማዊ ዐፄ ኀይለ ሥላሴ ቦታውን ይንከባከቡት የነበረ ሲሆን ለገዳሙ መርጃ የሚሆን አዲስ አበባ ላይ የሚከራይ ቤት አሠርተው በኪራዩ ገቢ ገዳሙ እንዲጠቀም አድርገው ነበር። በአካልም ገዳሙ ድረስ በመሔድ በረከትን ይቀበሉ ነበር።
#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_አሮን_ዘአርምም
መጽሐፍ አሮን ዘከትሞ ወዘአርምሞ ይላችዋል። የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ተንቤን ነው። ለ48 ዓመታት ከሰው ጋር ምንም ሳይነጋገሩ በዝምታ ብቻ የኖሩ ታላቅ አባት ሲሆኑ ቀዳማዊ ዘኢትዮጵያ ከተባሉት የመጀመርያዎቹ ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ናቸው። ቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑ ርግብ ዕጣን ታመጣላቸው ነበር። ምግባር ቱሩፋታቸው እጅግ ያማረው እኚህ አባት በዘመናቸው ድርቅ በሆነ ጊዜ የእህል እጦት ሆኖ ሕዝቡን ሰብስበው እግዚኦታ ካደረሱ በኋላ የሀገሩን ሁሉ ጎተራ በተአምራት በእህል ሞልተው አትረፍርፈውታል። በዚህም አስገራሚ ተአምራቸው ሕዝቡንም ከችግርና ከርሃብ አድነውታል።
አቡነ መድኃኒነ እግዚአ ዘደብረ በንኰል አህያቸውን የበላባቸውን አንበሳ በአህያው ምትክ ሰባት ዓመት ውኃ እንዳስቀዱት ሁሉ አቡነ አሮንም ነብርን ሰባት ዓመት ውኃ እያስቀዱ እንዲያገለግላቸው አድርገውታል። ሌሎች የዱር አራዊትም ያገለግሏቸው ነበር። በአንድ ወቅት በሀገሩ ድርቅ ሆኖ ሰው ግማሹ ተሰዶ ግማሹ ደክሞ ስለነበር ጻድቁ ግን የዱር አራዊትን ጠርተው ሠራተኛ አድርገው በማዘዝ ጥንቸልን ውኃ በማስቀዳት፣ ጅብን ጭቃ በማስረገጥ፣ አንበሳን በአናጺነት እንዲሠራ፣ ነብርን ደግሞ አቀባይ በማድረግ እያዘዙ በማሠራት በ #እመቤታችን ስም እጅግ አስደናቂ ቤተ ክርስቲያን መስከረም 10 ቀን ሠርተዋል። የአቡነ አሮን ዘአርምሞ የአንድነት ገዳማቸው ትግራይ ሽሬ ውስጥ ይገኛል።
#ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጥቅምት_16ና #ከገድላት_አንደበት)
BY አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር
Share with your friend now:
tgoop.com/amennnnnnnnnnnnnnnnnnnn/7748
