tgoop.com/IbnuMunewor/7901
Last Update:
14. በመውሊድ በዓላት የተከበሩ የአላህ ቤቶች በጭብጨባ፣ በውዝዋዜና በጭፈራ ክብራቸው ይረከሳል። ይሄ ደግሞ አላህ ከሃዲዎችን እንዲህ ሲል ከወቀሰባቸው ነገሮች ውስጥ ነው፡-
(وَمَا كَانَ صَلَاتُهُمۡ عِندَ ٱلۡبَيۡتِ إِلَّا مُكَآءٗ وَتَصۡدِيَةٗۚ)
{በቤቱ ዘንድም ስግደታቸው ማፏጨትና ማጨብጨብ እንጂ ሌላ አልነበረም።} [አልአንፋል፡ 35]
ሃያሉ ጌታ እንዲከበሩና ስሙ እንዲወሳባቸው ባዘዘባቸው መስጂዶች ውስጥ ድቤ መደብደብ፣ ማጨብጨብና መጨፈር በአራቱም መዝሀብ የተወገዘ እጅግ አስነዋሪ ተግባር ነው። ይህን ቆሻሻ ተግባር መቃረቢያ አድርጎ ማሰብ ደግሞ የለየለት ጥመት ነው። ኢብኑል ጀውዚይ፡ “ዳንስን ወደ ላቀው አላህ መቃረቢያ ነው ብሎ የሞገተ ሰው ከኢስላም እንደሚወጣ የዑለማዎች ኢጅማዕ ተቋጭቷል” ብሏል። [ሶይዱል ኻጢር፡ 168]
15. ብዙ የመውሊድ ዝግጅቶች የሴትና የወንድ ቅልቅል በብዛት አለባቸው። የብል -ግና መናሃሪያ እየሆኑም ነው። በእለቱ እቃ እያዞሩ የሚሸጡ ሰዎች ሲጋራ፣ ኮንዶምና መሰል ነገሮችን እንደሚይዙ ተጨባጭ መረጃ አለ። በአንዳንድ አካባቢዎች ሴተኛ አዳሪዎች መውሊድ በሚከበርበት አካባቢ የተለያዩ ነገሮችን ለመሸጥ በሚል ሽፋን ጊዜያዊ ዳስ በመቀለስ ለጥፋት እንደሚሰማሩ ከሰበሰብኳቸው መረጃዎች አረጋግጫለሁ።
መቅሪዚይ በ790 ሂጅሪያ በዒማዱል አንባኒ በተዘጋጀው መውሊድ ላይ የታዘበውን እንዲህ ሲል ይገልፀዋል፡- “ሜዳው በዓሊሞች እስከሚጨናነቅ ህዝብ ጎረፈ። በዚያች ሌሊት ሴቶችና ወጣቶች ከባለጌዎች ጋር በመቀላቀላቸው ምክንያት ብዙ አይነት ብልግናዎች ተፈፀሙ። ማለዳ ላይ ሌሊቱን የተጠጡ ከሃምሳ በላይ የአስካሪ መጠጥ እንስራዎች በዛውያው ዙሪያ በነበሩ እርሻዎች ውስጥ ተጥለው እንደተገኙ፣ በርካታ ደናግላንም ክብረ-ንፅህናቸው እንደተገሰሰ፣ በጣም ብዙ ገንዘብ የወጣባቸው ሻማዎችም እንደተለኮሱ እጅግ በርካታ መረጃ ወጥቷል። በማግስቱ ጧት አላህ የንፋስ ጥቃት ላከባቸውና ከቦታው የነበሩ ሰዎችን ፊታቸውን አፈር አለበሳቸው። ድንኳኖቹንም ቆራረጣቸው። አንድም ሰው ባህር መሳፈር አልቻለም። ከዚያን ጊዜ በኋላ መውሊድ አልተዘጋጀም።” [ዱረሩል ዑቁዲል ፈሪዳህ፡ 2/501]
16. የመውሊድ ጨፋሪዎች በውዝውዛኔና መሰል ነገሮች ሰውነታቸው ዝሎ ሌሊቱን ገፍተው ስለሚተኙ አብዛኞቹ የፈጅር ሶላትን የተወሰኑት ደግሞ ዙህርንም ጭምር አይሰግዱም። ለነገሩ ክፍለ - ሃገር ላይ አብዛኛው ታዳሚ ከነጭራሹ ሶላት ሰጋጅ አይደለም።
17. መውሊድ ለማክበር አገር አቋርጠው ረጃጅም ርቀቶችን የሚጓዙ ሰዎች ሞልተዋል። ነብዩ ﷺ ግን ለቢድዐ ቀርቶ ለአላህ ታስቦ ለሚፈፀመው አምልኮት እንኳን ከሶስቱ መስጂዶች (መስጂደል ሐራም፣ መዲና የነብዩ መስጂድ እና አቅሷ) ውጭ አገር አቋርጦ መጓዝ እንደማይገባ አሳስበዋል። [ቡኻሪ፡ 1189] [ሙስሊም፡ 3450] አገር አቋርጠው ያለ መሕረም የሚጓዙ ሴቶችም ቀላል አይደሉም። ነብዩ ﷺ ግን “ማንኛዋም ሴት ከቅርብ ወንድ ቤተሰቧ ጋር እንጂ እንዳትጓዝ” ብለዋል። [ቡኻሪ፡ 1862]
18. መውሊድ የልዩነት መንሰኤ ነው። ለዚህም መውሊድ በተቃረበ ቁጥር የሚነሳውን ውዝግብ መስማቱ ብቻ በቂ ነው። በመውሊድ ላይ ስላልተጋሯቸው ብቻ “ወሃ ~ ቢ”፣ “የነቢ ጠ ^ላት”፣ “ከአይ ^ ሁድ በከፋ ዲን ያበላሹ” እያሉ ሙስሊሞችን መወንጀል የተለመደ ዘመቻ ነው። ኢብኑ ተይሚያ ረሒመሁላህ እንደሚሉት “ቢድዐ ከልዩነት ጋር የተቆራኘ ነው።” ስለዚህ ቢድዐው እስካለ ድረስ መለያየቱ አይቀርም። ሸውካኒይ እንዲህ ይላሉ፡- “ደግሞም ይሄ መውሊድ ከተከሰተ በኋላ ውዝግቡ ተጧጡፏል። በዚህም ላይ የሚፃፉት ኪታቦች ከከልካዩም ከፈቃጁም በዝተዋል። … ከነሱ ውስጥ እንደማይፈቀድ ቁርጥ አድርጎ የተናገረ ሲኖር ከነሱ ቢድዐነቱን አምኖ መጥፎ ነገር ካልተቆራኘው በሚል መስፈርት የፈቀደው አለ፣ ምንም ማስረጃ ግን አላመጣም።” [አልፈትሑ ረባኒ፡ 2/1091-1095]
ጥፋቶቹ እነዚህ ብቻ አይደሉም። ይህን ሁሉ ጉድ አጭቆ የያዘ ቢድዐ ከጥቃቅን ነገሮች ነውን? ህሊና ያለው ይፍረድ። በርግጥ ከነዚህ ጥፋቶች ውስጥ ከፊሎቹን የሚርቁ አሉ። ግና አንደኛ ጥቂት ናቸው። ሁለትኛ እነዚህ እራሱ ድግሳቸውን በሺርክ የተቀላቀለ መንዙማ ባዮችን ይጋብዙበታል። ከሺርኩ ቢጠራም ድርጊቱ በራሱ መረጃ የለውምና ከቢድዐነት አይዘልም። ሶስተኛ በጥፋት የተወረረውን መውሊድ ሊያወግዙ ቀርቶ የሚያወግዙትን የሚነቅፉ ናቸው። ስለሆነም ጥፋታቸው ከነዚያኞቹ ጥፋት ብዙም የራቀ አይደለም።
=
ኢብኑ ሙነወር
የቴሌግራም ቻናል፦
https://www.tgoop.com/IbnuMunewor
https://www.tgoop.com/IbnuMunewor
BY Ibnu Munewor (ኢብኑ ሙነወር)


Share with your friend now:
tgoop.com/IbnuMunewor/7901