tgoop.com/IbnuMuhammedzeyn/1562
Last Update:
ስንፍና እሹሩሩ
~
ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ከሚታዩ አስቀያሚ ሃሳቦች አንዱ "እኔ ረጅም ፅሑፍ አልወድም" የሚል የስንፍና አዋጅ ነው። ደግሞኮ በዚህ በሽታ የተለከፈው ብዛቱ! ለምን ግን ነውር ጌጡ እንሆናለን? ሁለት ሶስት ገፅ ፅሑፍ ረዝሞ ነው "ረጅም ፅሑፍ" እያልን የምንገልፀው? ደግሞስ አለማንበብ ቁምነገር ሆኖ ነው እንደ ጀብድ የምናወራው? እኛ በዚህ ዓይነት ገዳይ ስንፍና ውስጥ ከሆንን ማነው ልጆቻችንን መስመር የሚያሲዛቸው? እንዴትስ ነው ከልብ ሆነው ኪታብ እንዲቀሩ፣ ትምህርት እንዲማሩ የምናደርጋቸው? ለመሆኑ ክፉ ምሳሌ እንዳንሆን ቦታ እየመረጥን ነው "ረጅም ፅሑፍ አልወድም" የምንለው? ነው ወይስ ለታዳጊዎችም ስንፍናችንን "በክብር" እያወረስን ነው?
እንዲያው ክፉ በሽታ ቢጣባን እንጂ እንደ ማንበብ የሚያረካ ምን አለ? እንዴት ነው ሳናነብ የአስተሳሰብ አድማሳችንን የምናሰፋው? እንዴት ነው ያለ ንባብ ራሳችንን የምንለውጠው? እንዴት ነው ያለ ንባብ ትውልድ የምንገነባው? ጭራሽ ባደባባይ ተወጥቶ "እኔ ረጅም ፅሑፍ አልወድም" እያሉ እንደ ጀብድ ይቀባበሉታል። እሺ አትወድም። ሰው ነውሩን ባደባባይ ያሰጣል? "የንባብ ባህላችን ሞተ ምን ይሻላል?"፣ "የንባብ ፍቅር የለኝም፤ ምን ባደርግ ይሻለኛል?" የሚል ሰው መፍትሄ ፍለጋ ይናገር። "እንዴት ችግሬን ልቅረፍ?" ለማለት። በጋራ መፍትሄ ለመፈለግ። ዛሬ የሚታየው ግን ሌላ ነው። አንዱ "እኔ ረጅም ፅሑፍ አልወድም" ሲል ሌሎችም እንደ ቁም ነገር እያከታተሉ "እኔም"፣"እኔም" እያሉ የኮሜንት ዶፍ ያወርዳሉ። ይሄ ነውር ነው፤ ነውር ጌጡ! ለአኺራም ይሁን ለዱንያ የሚሆኑ ቁምነገር አዘል ዳጎስ ያሉ ኪታቦችንና መፅሐፎችን ማንበቡ ቀርቶ ጭራሽ ሶስትና አራት ገፆችን ለማንበብ ልባቸው ጉሮሯቸው ስር ይወተፋል። ከዚያ ህፃን ይመስል ፕራንክ እያሯሯጡ፣ እንቶፈንቶ የቴክቶክና የዩቲዩብ ቪዲዮ እያሳደዱ ይውላሉ። ይሄ ሊታከሙት የሚገባ በሽታ ነው። ሰው እንዴት ፕራንክ የሚሉት የጅላጅል ስራ ላይ ሲያገጥ ይውላል? ሱብሓነላህ!
በተለይ ጦለበተል ዒልም (ደረሶች) እንዴት ነው ኪታብ ሳታነቡ የምትውሉት? እስኪ በዚህ አመት ስንት ኪታብ እንዳነበብክ ራስህን መለስ ብለህ ታዘበው? የዒልም ጉዞህ እንዲህ የተንዘላዘለ እንዲሆን ነው የምትፈልገው? ትርጉም ያለው የዒልም ትጥቅ መታጠቅ የሚፈልግ ሰው እንዴት ያለ ንባብ ካሰበበት እደርሳለሁ ብሎ ያስባል?! ይሄ የግድ መታረም ያለበት ክፉ ልማድ ነው።
ለማንኛውም ነፍስ እንደ ያዟት ነው የምትሆነው። ለቁርኣን ጊዜ የማይሰጥ ሰው 30 ደቂቃ ቁጭ ብሎ መቅራት ትእግስቱን ይፈታተነዋል። ከሶላት ጋር ልቡ ያልተዋሀደ ሰው አራት ረከዐ ለመስገድ አስሬ ያዛጋል። ችግሩን ለመፍታት ግን ከአላህ ጋር ቀላል ነው። በቅድሚያ የችግሩን አሳሳቢነት እንመን። ከዚያ ቁርጠኝነት እንታጠቅ። ከዚያ ተደጋጋሚ ጥረት እናድርግ። ከዚያ ለውጣችንን እንገምግም። አንዴ ህይወታችን ጋር ከተዋሀደ ወላሂ እያጣጣምነው ነው የምንኖረው። ስንፍናችንን እሹሩሩ እያልን የምንቀጥል ከሆነ ግን እድሜ ልካችንን በድንቁርና እያጌጥን ነው የምንኖረው። አላህ ይሁነን።
=
የቴሌግራም ቻናል፡-
https://www.tgoop.com/IbnuMunewor
BY Ibnu Muhammedzeyn
Share with your friend now:
tgoop.com/IbnuMuhammedzeyn/1562