tgoop.com/Enatachn_mareyam/18296
Last Update:
🕊
[ † እንኳን ለታላቁ ነቢይ ቅዱስ ኢያሱ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፣ አደረሰን። † ]
† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ! †
🕊 † ቅዱስ ኢያሱ ነቢይ ወመስፍን † 🕊
† ቅዱሱ የተወለደው በምድረ ግብፅ በባርነት ከነበሩ እሥራኤላውያን ሲሆን የቀደመ ስሙ "አውሴ" ይባላል:: ዘመኑ እግዚአብሔር ሕዝቡን ከ፪፻፲፭ [215] ዓመታት ባርነት ሊያወጣ የተቃረበበት ነውና ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከምድያም ሲመለስ ከመረጣቸው ተከታዮቹ ዋነኛው ኢያሱ ነበር:: እሥራኤል ከባርነት ሲወጡ ሙሴ ፹ [80] ዓመቱ : ኢያሱ ደግሞ ፵ [40] ዓመቱ ነበር::
ሕዝቡ አንገተ ደንዳና ነበርና ለ፵ [40] ቀን የታሠበላቸውን መንገድ ፵ [40] ዓመት እንዲሆን አደረጉት:: በዚህ ጊዜ ኢያሱ ከመምሕሩ ከሙሴና ከሕዝቡ አልተለየም::
አውሴን "ኢያሱ" ብሎ ስም የቀየረለት ሙሴ ሲሆን ይሔውም በፈቃደ እግዚአብሔር ነው:: ኢያሱ ማለት "መድኃኒት" ማለት ነው:: ለዚሕም ምክንያቶች አሉት:- ለጊዜው አማሌቃውያንን ድል ነስቶ ሕዝቡን አድኗል:: ምድረ ርስትን አውርሷል:: ለፍጻሜው ግን ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ [ጥላ] እንዲሆን ነው::
ቅዱስ ኢያሱ በበርሃ ለ፵ [40] ዘመናት እግዚአብሔርን አምልኮታል:: ሊቀ ነቢያትን ታዝዞታል [አገልግሎታል]:: እሥራኤልንም የጦር አለቃ ሆኖ ከአሕዛብ እጅ አድኗቸዋል::
በዚህም በእግዚአብሔርና በሕዝቡ ዘንድ ሞገስን አግኝቷል:: ቅዱስ ሙሴ ደብረ ናባው ላይ ባረፈ ጊዜ ሕዝቡን : ካሕናቱንና ታቦተ ጽዮንን ተረከበ:: ይህን ጊዜ ዕድሜው ፹ [80] እየሆነ ነበር::
† እግዚአብሔርም ኢያሱን "ከአንተ ጋር ነኝ" ብሎ በሕዝቡ ላይ ነቢይና መስፍን [አስተዳዳሪ] እንዲሆን ሾመው:: ቅዱሱም ሰላዮችን ልኮ አስገምግሞ:
¤ ባሕረ ዮርዳኖስን ከፍሎ
¤ ሕዝቡን አሻግሮ
¤ የኢያሪኮን ቅጥር ፯ [ 7 ] ጊዜ ዙሮ
¤ በኃይለ እግዚአብሔር አፍርሶ
¤ የኢያሪኮን ነገሥታት አጥፍቶ ለሕዝቡ ምድረ ርስትን አወረሰ::
የገባዖን ሰዎች "አድነን" ብለው በላኩበት ጊዜ ነገሥተ አሞሬዎንን ይወጋ ዘንድ ኢያሱ ወጣ:: እነዚያን ግሩማን ነገሥታት በፈጣሪው ኃይል : በጦርና በተአምራት ድል ነስቶ የእግዚአብሔር ስሙ ከፍ ከፍ አለ:: በዚያች ዕለትም ለ፲፪ [12] ቱ ነገደ እሥራኤል ርስትን ሲያካፍል ፀሐይን በገባዖን: ጨረቃን ደግሞ በቆላተ ኤሎም [በኤሎም ሸለቆ] አቆመ::
ሰባት አሕጉራተ ምስካይ [የመማጸኛ ከተሞችን] ለየ:: ነቢይና መስፍን ሆኖ ሕዝቡን ለ፵ [40] ዓመታት አገለገለ:: በመጨረሻም ለሕዝቡ አላቸው :-
"እኔና ቤቴ እግዚአብሔርን እናመልካለን:: [ኢያ.፳፬] (24) እናንተስ?" አላቸው:: እነርሱም "እኛም እንዳንተ ነን" አሉት:: ለዚህም ምልክት ይሆን ዘንድ ፫ [3] ገጽ ያላት ሐውልትን በመካከላቸው አቆመ::
ይህችውም የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት:: ሐውልቷ ፫ [3] ገጽ እንዳላት እመቤታችንም በ፫ [3] ወገን [በነፍስ: በሥጋ: በልቡና] ድንግል ናት:: አንድም በ፫ [3] ወገን [ከኃልዮ: ከነቢብ: ከገቢር ኃጢአት] ንጽሕት ናት:: ለዚህም ነው አባ ሕርያቆስ "ሐውልተ ስምዕ ዘኢያሱ" [የኢያሱ የምስክር ሐውልት አንቺ ነሽ] ሲል ያመሰገናት::
ታላቁ ነቢይ ኢያሱ ግን ከግብጽ በወጡ በ፹ [80] ዓመት: በተወለደ በ፻፳ [120] ዓመቱ [ጥሬው መጽሐፍ ቅዱስ በ፻፲ [110] ዓመቱ ይላል] በወገኖቹ መካከል ዐርፎ በያዕቆብ መቃብር ተቀበረ:: እሥራኤልም ለ፴ [30] ቀናት አለቀሱለት::
† በወዳጁ በኢያሱ እጅ የአሕዛብን ቅጥር ያፈረሰ እግዚአብሔር የእኛንም የኃጢአታችንን ግንብ በወዳጆቹ ምልጃ ያፍርስልን:: ከቅዱሱ ነቢይም በረከትን ያሳትፈን::
🕊
[ † ሰኔ ፳፮ [ 26 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]
፩. ቅዱስ ኢያሱ ነቢይ ወመስፍን
፪. ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት [ቅዳሴ ቤቱ]
[ † ወርሐዊ በዓላት ]
፩. ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
፪. አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
፫. አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
፬. ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
፭. አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
† " አሁንም እግዚአብሔርን ፍሩ:: በእውነተኛም ልብ አምልኩት . . . እግዚአብሔርን ማምለክ ክፉ መስሎ ቢታያችሁ . . . የአሞራውያንን አማልክት ታመልኩ እንደ ሆነ: የምታመልኩትን ዛሬ ምረጡ:: እኔና ቤቴ ግን እግዚአብሔርን እናመልካለን::" † [ኢያሱ.፳፬፥፲፬] (24:14)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †
[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]
† † †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖 🕊 💖
BY አብሰራ ገብርኤል ለማርያም
Share with your friend now:
tgoop.com/Enatachn_mareyam/18296