Telegram Web
#የኅዳር_22_ግጻዌ

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ኅዳር_22_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ቆሮ 7
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ እንግዲህ፥ ወዳጆች ሆይ፥ የዚህ ተስፋ ቃል ካለን፥ በእግዚአብሔር ፍርሃት ቅድስናን ፍጹም እያደረግን ሥጋንና መንፈስን ከሚያረክስ ሁሉ ራሳችንን እናንጻ።
² በልባችሁ ስፍራ አስፉልን፤ ማንንም አልበደልንም፥ ማንንም አላጠፋንም፥ ማንንም አላታለልንም።
³ ለኵነኔ አልልም፤ በአንድነት ለመሞትና በአንድነት ለመኖር በልባችን እንዳላችሁ አስቀድሜ ብዬአለሁና።
⁴ ስለ እናንተ እምነቴ ታላቅ ነው፥ በእናንተ ምክንያት ትምክህቴ ታላቅ ነው፤ መጽናናት ሞልቶብኛል፤ በመከራችን ሁሉ ደስታዬ ከመጠን ይልቅ ይበዛል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ያዕቆብ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²-³ ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት
⁴ ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም።
⁵ ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል።
⁶ ነገር ግን በምንም ሳይጠራጠር በእምነት ይለምን፤ የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባሕርን ማዕበል ይመስላልና።
⁷-⁸ ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው።
⁹-¹⁰ የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና።
¹¹ ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል።
¹² በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።
¹³ ማንም ሲፈተን፦ በእግዚአብሔር እፈተናለሁ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም።
¹⁴ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል።
¹⁵ ከዚህ በኋላ ምኞት ፀንሳ ኃጢአትን ትወልዳለች፤ ኃጢአትም ካደገች በኋላ ሞትን ትወልዳለች።
¹⁶ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ አትሳቱ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 17
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
² ጳውሎስም እንደ ልማዱ ወደ እነርሱ ገባ፥ ሦስት ሰንበትም ያህል ከእነርሱ ጋር ከመጻሕፍት እየጠቀሰ ይነጋገር ነበር፤
³ ሲተረጉምም ክርስቶስ መከራ እንዲቀበልና ከሙታን እንዲነሣ ይገባው ዘንድ እያስረዳ፦ ይህ እኔ የምሰብክላችሁ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ነው ይል ነበር።
⁴ ከእነርሱም አንዳንዶቹ ተረድተው ከሚያመልኩም ከግሪክ ሰዎች ብዙ ከከበሩትም ሴቶች ጥቂቶች ያይደሉ፥ ከጳውሎስና ከሲላስ ጋር ተባበሩ።
⁵ አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ ሕዝብንም ሰብስበው ከተማውን አወኩ፥ ወደ ሕዝብም ያወጡአቸው ዘንድ ፈልገው ወደ ኢያሶን ቤት ቀረቡ፤
⁶ ባላገኙአቸውም ጊዜ ኢያሶንንና ከወንድሞች አንዳንዶችን ወደ ከተማው አለቆች ጎትተው፦ ዓለምን ያወኩ እነዚህ ወደዚህ ደግሞ መጥተዋል፥ ኢያሶንም ተቀብሎአቸዋል፤
⁷ እነዚህም ሁሉ፦ ኢየሱስ የሚሉት ሌላ ንጉሥ አለ እያሉ የቄሣርን ትእዛዝ ይቃወማሉ ብለው ጮኹ።
⁸ ሕዝቡና የከተማውም አለቆች ይህን ነገር በሰሙ ጊዜ ታወኩ፥
⁹ ከኢያሶንና ከሌሎቹም ዋስ ተቀብለው ለቀቁአቸው።
¹⁰ ወዲያውም ወንድሞች ጳውሎስንና ሲላስን በሌሊት ወደ ቤርያ ሰደዱአቸው፥ በደረሱም ጊዜ ወደ አይሁድ ምኵራብ ገቡ፤
¹¹ እነዚህም በተሰሎንቄ ከሚኖሩት ይልቅ ልበ ሰፊዎች ነበሩና፦ ነገሩ እንደዚሁ ይሆንን? ብለው ዕለት ዕለት መጻሕፍትን እየመረመሩ ቃሉን በሙሉ ፈቃድ ተቀበሉ።
¹² ስለዚህም ከእነርሱ ብዙ፥ ከግሪኮችም የከበሩት ሴቶችና ወንዶች ጥቂት ያይደሉ፥ አመኑ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኅዳር_22_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አዕይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባዕ ቅድሜከ ገዐሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ.78፥10-11።

#ትርጉም፦ "አሕዛብ፦ አምላካቸው ወዴት ነው? እንዳይሉ፥ የፈሰሰውን የባሪያዎችህን ደም በቀል በዓይኖቻችን ፊት አሕዛብ ይወቁ።
የእስረኞች ጩኸት ወደ ፊትህ ይግባ፤ እንደ ክንድህም ታላቅነት ሊገደሉ የተፈረደባቸውን አድን"። መዝ.78፥10-11።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኀዳር_22_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 9
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁰ በቤቱም በማዕድ ተቀምጦ ሳለ፥ እነሆ፥ ብዙ ቀራጮችና ኃጢአተኞች መጥተው ከኢየሱስና ከደቀ መዛሙርቱ ጋር አብረው ተቀመጡ።
¹¹ ፈሪሳውያንም አይተው ደቀ መዛሙርቱን፦ መምህራችሁ ከቀራጮችና ከኃጢአተኞች ጋር አብሮ ስለ ምን ይበላል? አሉአቸው።
¹² ኢየሱስም ሰምቶ፦ ሕመምተኞች እንጂ ባለ ጤናዎች ባለ መድኃኒት አያስፈልጋቸውም፤
¹³ ነገር ግን ሄዳችሁ፦ ምሕረትን እወዳለሁ መሥዋዕትንም አይደለም ያለው ምን እንደ ሆነ ተማሩ፤ ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁምና አላቸው።
¹⁴ በዚያን ጊዜ የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ወደ እርሱ ቀርበው፦ እኛና ፈሪሳውያን፥ ብዙ ጊዜ የምንጦመው፥ ደቀ መዛሙርትህ ግን የማይጦሙት ስለ ምንድር ነው? አሉት።
¹⁵ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ ሚዜዎች ሙሽራው ከእነርሱ ጋር ሳለ ሊያዝኑ ይችላሉን? ነገር ግን ሙሽራው ከእነርሱ የሚወሰድበት ወራት ይመጣል፥ በዚያ ጊዜም ይጦማሉ።
¹⁶ በአረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና፥ መቀደዱም የባሰ ይሆናል።
¹⁷ በአረጀ አቁማዳ አዲስ የወይን ጠጅ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን፥ አቁማዳው ይፈነዳል፥ የወይን ጠጁም ይፈሳል አቁማዳውም ይጠፋል፤ ነገር ግን አዲሱን የወይን ጠጅ በአዲስ አቁማዳ ያኖረዋል፥ ሁለቱም ይጠባበቃሉ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
✝️የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱስ_ዮሐንስ_ወልደ_ነጎድጓድ_ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ኅዳር_23

#አንድ_አምላክ_በሆነ_በአብ_በወልድ_በመንፈስ_ቅዱስ ስም
ኅዳር ሃያ ሦስት በዚች ቀን የመቶ አለቃ የነበረ #ጻድቁ_ቅዱስ_ቆርኔሌዎስ አረፈ፣ #የነቢይ_አብድዩም የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ጻድቁ_ቅዱስ_ቆርኔሌዎስ (የመቶ አለቃው)

ኅዳር ሃያ ሦስት በዚች ቀን የመቶ አለቃ የነበረ ጻድቁ ቆርኔሌዎስ አረፈ። ይህም ቅዱስ የፍልስጥዔም ክፍል በሆነች በቂሣርያ የመቶ አለቃ ሁኖ የተሾመ ነው። እርሱም ከዋክብትን ሲያመልክ ነበር እንደርሱ ማንም ሊአደርግ የማይቻለውን የሚያመልካቸው አማልክቶቹም ቢሆኑ በሐዋርያት እጅ የሚደረገውን የተአምራታቸውንና የስብከታቸውን ዜና በሰማ ጊዜ ወዲያውኑ ለአማልክት መስገድን ተወ።

ከዚህም በኋላ የሚጾም የሚጸልይ ለድኆችና ለችግረኞች የሚመጸውት ሆነ በጸሎቱም ጊዜ እንዲህ ይል ነበር አቤቱ አምላክ ሆይ እኔ አንተን ከማወቅ ጎደሎነኝና አንተ ግን የቀና መንገድህን ምራኝ።

ቸር ይቅር ባይ #እግዚአብሔርም ይቅር ብሎት መልአኩን ላከለት ወደርሱም አይቶ ቆርኔሌዎስ ፈራ አቤቱ ምን ትላለህ አለ ጸሎትህ ምጽዋትህ መልካም መታሰቢያ ሆኖ ወደ #እግዚአብሔር ዐርጓል አሁንም በጫማ ሰፊው በስምዖን ቤት የሚኖረውን ስምዖን ጴጥሮስን ይጠሩልህ ዘንድ ሰዎችን በባሕር አቅራቢያ ወደአለች ኢዮጴ ከተማ ላክ አለው።

በዚያንም ጊዜ መልአኩ እንደነገረው ሰዎችን ላከ ጴጥሮስም በመጣ ጊዜ ቆርኔሌዎስ ተቀብሎ ከእግሩ በታች ሰገደለት ቅዱስ ጴጥሮስም አነሣውና ተነሥ እኔም እንዳንተ ሰው ነኝ አለው። ከእርሱም ጋር እየተነጋገረ ገባ ወደርሱም የመጡ ብዙ ሰዎችን አገኘ።

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው ለአይሁዳዊ ሰው ሒዶ ከባዕድ ወገን ጋር መቀላቀል እንደማይገባው ታውቃላችሁ እኔን ግን ማንንም ማን ቢሆን እንዳልጸየፍ #እግዚአብሔር አሳየኝ። አሁንም እንደላካችሁብኝ ሳልጠራጠር ወደ እናንተ መጣሁ የጠራችሁኝ ለምን እንደሆነ እስቲ ንገሩኝ።

ቅዱስ ቆርኔሌዎስም ዛሬ አራተኛ ቀን ነው አለ በቤቴ ውስጥ በዘጠኝ ሰዓት ስጸልይ አንድ ሰው ብርሃን ለብሶ ታየኝ። እንዲህም አለኝ ቆርኔሌዎስ ጸሎትህ ተሰማ ምጽዋትህም በ #እግዚአብሔር ፊት ታሰበልህ ። አሁንም ከባሕር አቅራቢያ ወዳለችው ወደ ኢዮጴ ከተማ ላክና በጫማ ሰፊው በስምዖን ቤት የሚኖረውን ጴጥሮስ የተባለ ስምዖንን ይጥሩልህ እርሱ አንተ የምትድንበትን ወገኖችህም ሁሉ የሚድኑበትን ይነግርሃል።

ያን ጊዜም ስለዚህ ወዳንተ ላክሁ ወደእኛ መምጣትህም መልካም አደረግህ አሁንም #እግዚአብሔር ያዘዘህን ሁሉ ልንሰማ እነሆ ሁላችን በፊትህ አለን።

ቅዱስ ጴጥሮስም አንደበቱን ገልጦ ስለ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስለ ዓለሙ ሁሉ ድኅነት ሰው መሆኑን መከራ ተቀብሎም ተሰቅሎ ስለ መሞቱ ስለ መነሣቱና ወደ ሰማይ ስለማረጉ ዳግመኛም በሕያዋንና በሙታን ላይ ለመፍረድ ስለ መምጣቱ አስተማራቸው።

የከበረ ቆርኔሌዎስም ከቤተሰቦቹ ሁሉ ጋር ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አመነ ከዚያ የነበሩ ብዙዎች አሕዛብም አመኑ በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍም እንደተጻፈ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም ተጠመቁ።

ከዚህም በኋላ ቆርኔሌዎስ ይህን ዓለም ለመግዛት የተሾመውን ሹመት ተወ ቅዱስ ጴጥሮስ ለ #ክርስቶስ ጭፍራ የመሆንን ሹመት በመስጠት ለእስክንድርያ አገር ኤጲስቆጶስነት ሹሞታልና ወደ ርሷም ሒዶ ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስም ሰበከ ጣዖታትንም ለሚያመልኩ ስሕተት መሆኑን ገለጠላቸው ልባቸውንም #እግዚአብሔርን በማወቅ ብሩህ አደረገላቸው በፊታቸውም ተአምራትን አደረገ ብዙዎችም አምነው ተጠመቁ ከእነርሱም በኋላ መኰንኑን ድሜጥሮስን አጠመቀው። #እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ነቢዩ_ቅዱስ_አብድዩ

በዚችም ዕለት ዳግመኛ የስሙ ትርጓሜ የ #እግዚአብሔር አገልጋይ የሆነ የነቢይ አብድዩ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው ።

በመጽሐፍ ቅዱስ 1ኛ ነገ. 18፥3 ላይ "አብደዩ #እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር" ተብሎ የተነገረለት እውነትም "የ #እግዚአብሔር አገልጋይ" የሆነ የነቢዩ ቅዱስ ኤልያስ ደቀ መዝሙር የነበረ ታላቅ ነቢይ ነው፡፡

ነቢዩ አብድዩ ነገዱ ከነገደ ኤፍሬም ሲኾን አባቱ አኪላ እናቱም ሳፍጣ እንደሚባሉ የቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ያስረዳል፡፡ ይህም ቅዱስ ነቢይ ከጠረፍ በረሃ አቅራቢያ ካለች ሱሳም በምትባል አገር ካሉ ሰዎች ወገን ነው፡፡ ለነቢዩ ቅዱስ ኤልያስ ደቀ መዝሙሩ ሆኖ በንጉሡ በአክዓብምና በንግሥቲቱ በኤልዛቤል ምክንያት በእርሱ ላይ የመጣውን መከራ ሁሉ ታግሷል፡፡ ታላቁ ነቢይ ቅዱስ ኤልያስ ከእነ ኤልዛቤል ሸሽቶ ወደ ተራራ ላይ ወጥቶ በዋሻ ተሸሽጎ ምግቡን አሞራ እያመጣለት በኖረበት ጊዜ እንኳን አብድዩ ግን ብቻውን የ #እግዚአብሔርን ነቢያት ይንከባከብ ነበር፡፡ ቅዱስ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥ የነበረ ቢሆንም ንግሥት ኤልዛቤል የ #እግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ ቅዱስ አብድዩ መቶውን ነቢያት ወስዶ አምሳ አምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው የነበረ ታላቅ ባለውለታ ነው፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ታሪኩ እንዲህ ተብሎ ነው የተጻፈው፡- "ከብዙ ቀንም በኋላ በሦስተኛው ዓመት "ሂድ ለአክዓብ ተገለጥ፥ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ" የሚል የ #እግዚአብሔር ቃል ወደ ኤልያስ መጣ፡፡ ኤልያስም ለአክዓብ ይገለጥ ዘንድ ሄደ፤ በሰማርያም ራብ ጸንቶ ነበር፡፡ አክዓብም የቤቱን አዛዥ አብድዩን ጠራ፤ አብድዩ #እግዚአብሔርን እጅግ ይፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤልም የ #እግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ እርሱ መቶውን ነቢያት ወስዶ አምሳ አምሳውን በዋሻ ውስጥ ሸሽጎ እንጀራና ውኃ ይመግባቸው ነበር፡፡ አክዓብም አብድዩን "በአገሩ መካከል ወደ ውኃው ምንጭ ሁሉና ወደ ወንዝ ሁሉ ሂድ፤ እንስሶችም ሁሉ እንዳይጠፉ ፈረሶችንና በቅሎችን የምናድንበት ሣር ምናልባት እናገኛለን" አለው፡፡

ሁለቱም የሚመለሱበትን አገር ተካፈሉ፤ አክዓብም ለብቻው በአንድ መንገድ አብድዩም ለብቻው በሌላ መንገድ ሄዱ፡፡ አብድዩም በመንገድ ሲሄድ እነሆ ቅዱስ ኤልያስ ተገናኘው፤ አብድዩም አወቀው፣ በግምባሩም ተደፍቶ "ጌታዬ ሆይ! ኤልያስ አንተ ነህን?" አለ፡፡ ቅዱስ ኤልያስም "እኔ ነኝ ሄደህ ለጌታህ ‹ኤልያስ ተገኝቶአል› በል አለው፡፡ ቅዱስ አብድዩም "እኔን ባሪያህን እንዲገድል በአክዓብ እጅ አሳልፈህ ትሰጠኝ ዘንድ ምን ኃጢአት አድርጌአለሁ? አምላክህ ሕያው #እግዚአብሔርን! ጌታዬ ይፈልግህ ዘንድ ያልላከበት ሕዝብ ወይም መንግሥት የለም፤ ሁሉም 'በዚህ የለም' ባሉ ጊዜ አንተን እንዳላገኙ መንግሥቱንና ሕዝቡን አምሎአቸው ነበር፡፡ አሁንም እነሆ 'ሂድ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር' ትለኛለህ፡፡ እኔም ከአንተ ጥቂት ራቅ ስል የ #እግዚአብሔር መንፈስ አንሥቶ ወደማላውቀው ስፍራ ይወስድሃል፤ እኔም ገብቼ ለአክዓብ ስናገር ባያገኝህ ይገድለኛል፤ እኔም ባሪያህ ከትንሽነቴ ጀምሬ #እግዚአብሔርን እፈራ ነበር፡፡ ኤልዛቤል የ #እግዚአብሔርን ነቢያት ባስገደለች ጊዜ መቶውን የ #እግዚአብሔር ነቢያት ወስጄ አምሳ አምሳውንም በዋሻ ውስጥ ሸሽጌ እንጀራና ውኃ የመገብኋቸው ነበር፡፡ ይህ ያደርግሁት ነገር በውኑ ለጌታዬ አልታወቀህምን? አሁንም 'ሄደህ ኤልያስ ተገኘ ብለህ ለጌታህ ንገር ትላለህ' እርሱም ይገድለኛል" አለው፡፡
ቅዱስ ኤልያስም ''በፊቱ የቆምሁት የሠራዊት ጌታ ሕያው #እግዚአብሔርን! እኔ ዛሬ ለእርሱ እገለጣለሁ" አለ፡፡ ቅዱስ አብድዩም አክዓብን ሊገናኘው ሄደ፣ ነገረውም፤ አክዓብም ኤልያስን ሊገናኘው መጣ፡፡ አክዓብም ኤልያስን ባየው ጊዜ "እስራኤልን የምትገለባብጥ አንተ ነህን?" አለው፡፡ ኤልያስም "እስራኤልን የምትገለባብጡ የ #እግዚአብሔርን ትእዛዝ ትታችሁ በኣሊምን የተከተላችሁ፣ አንተና የአባትህ ቤት ናችሁ እንጂ እኔ አይደለሁም" አለው፡፡ 1ኛ ነገ.18፥1-20፡፡

ቅዱስ አብድዩ የንጉሥ አክዓብ የቤቱን አዛዥነቱን ትቶ የቅዱስ ኤልያስ ቀደ መዝሙሩ ሆኖ በነቢይነት #እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖሮ የትንቢቱ ወራት ሲፈጸም በዚህች ዕለት ዐርፏል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ኅዳር_23 እና #ከገድላት_አንደበት)
#የኅዳር_23_ግጻዌ

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ኅዳር_23_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዕብራውያን 11
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³² እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና።
³³ እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥
³⁴ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ።
³⁵ ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤
³⁶ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤
³⁷ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤
³⁸ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ።
³⁹-⁴⁰ እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ጴጥሮስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁹ ከእርሱም ይልቅ እጅግ የጸና የትንቢት ቃል አለን፤ ምድርም እስኪጠባ ድረስ የንጋትም ኮከብ በልባችሁ እስኪወጣ ድረስ፥ ሰው በጨለማ ስፍራ የሚበራን መብራት እንደሚጠነቀቅ ይህን ቃል እየጠነቀቃችሁ መልካም ታደርጋላችሁ።
²⁰ ይህን በመጀመሪያ እወቁ፤ በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም፤
²¹ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²³ እርሱም ወደ ውስጥ ጠርቶ እንድግድነት ተቀበላቸው። በነገውም ተነሥቶ ከእነርሱ ጋር ወጣ፥ በኢዮጴም ከነበሩት ወንድሞች አንዳንዶቹ ከእርሱ ጋር አብረው ሄዱ።
²⁴ በነገውም ወደ ቂሣርያ ገቡ፤ ቆርኔሌዎስም ዘመዶቹንና የቅርብ ወዳጆቹን በአንድነት ጠርቶ ይጠባበቃቸው ነበር።
²⁵ ጴጥሮስም በገባ ጊዜ ቆርኔሌዎስ ተገናኝቶ ከእግሩ በታች ወደቀና ሰገደለት።
²⁶ ጴጥሮስ ግን፦ ተነሣ፤ እኔ ራሴ ደግሞ ሰው ነኝ ብሎ አስነሣው።
²⁷ ከእርሱም ጋር እየተነጋገረ ገባ፥ ብዙዎችም ተከማችተው አግኝቶ፦
²⁸ አይሁዳዊ ሰው ከሌላ ወገን ጋር ይተባበር ወይም ይቃረብ ዘንድ እንዳልተፈቀደ እናንተ ታውቃላችሁ፤ ለእኔ ግን እግዚአብሔር ማንንም ሰው ርኵስና የሚያስጸይፍ ነው እንዳልል አሳየኝ፤
²⁹ ስለዚህም ደግሞ ብትጠሩኝ ሳልከራከር መጣሁ። አሁንም በምን ምክንያት አስመጣችሁኝ? ብዬ እጠይቃችኋለሁ አላቸው።
³⁰ ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለው፦ በዚች ሰዓት የዛሬ አራት ቀን የዘጠኝ ሰዓት ጸሎት በቤቴ እጸልይ ነበር፤ እነሆም፥ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ ሰው በፊቴ ቆመና፦
³¹ ቆርኔሌዎስ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ ምጽዋትህም ታሰበ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኅዳር_23_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወበኀቤየሰ ፈድፋደ ክቡራን አዕርክቲከ እግዝኦ። ወፈድፋደ ፀንዑ እምቀደምቶሙ። እምኌቆሙ እምኆፃ ይበዝኁ"።  መዝ 138፥17-18።

#ትርጉም፦ "አቤቱ፥ አሳቦችህ በእኔ ዘንድ እንደ ምን እጅግ የተከበሩ ናቸው! ቍጥራቸውም እንደ ምን በዛ! ብቈጥራቸው ከአሸዋ ይልቅ ይበዛሉ፤ ተነሣሁም፥ እኔም ገና ከአንተ ጋር ነኝ"። መዝ 138፥17-18።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኅዳር_23_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³² ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤
³³ በሰው ፊትም የሚክደኝን ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እክደዋለሁ።
³⁴ በምድር ላይ ሰላምን ለማምጣት የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ሰይፍን እንጂ ሰላምን ለማምጣት አልመጣሁም።
³⁵ ሰውን ከአባቱ፥ ሴት ልጅንም ከእናትዋ፥ ምራትንም ከአማትዋ እለያይ ዘንድ መጥቻለሁና፤
³⁶ ለሰውም ቤተ ሰዎቹ ጠላቶች ይሆኑበታል።
³⁷ ከእኔ ይልቅ አባቱን ወይም እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም፤ ከእኔ ይልቅም ወንድ ልጁን ወይም ሴት ልጁን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም፤
³⁸ መስቀሉንም የማይዝ በኋላዬም የማይከተለኝ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።
³⁹ ነፍሱን የሚያገኝ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም ስለ እኔ የሚያጠፋ ያገኛታል።
⁴⁰ እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል።
⁴¹ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፥ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱስ_ዮሐንስ_ወልደ_ነጐድጓድ_ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ቆርኔሌዎስና የነቢዩ የቅዱስ አብድዩ የዕረፍታቸው በዓልና የነቢያት (የገና) የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ትንቢተ_አብድዩ

➛ትንቢተ አብድዩ ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት በጣም ትንሿና ፳፩ ቊጥሮችን ብቻ የያዘች ባለ ፩ ምዕራፍ መጽሐፍ ነች፡፡ ነገር ግን ትንሽ ስለኾነች #እግዚአብሔር ወደ እኛ እንዳትደርስ አላደረጋትም፡፡

የመጽሐፏ ዋና ዓላማም በኤዶምያስ ላይ ስለሚመጣው ፍርድ መናገር ነው፡፡ ኤዶምያስ ማለት ደግሞ በጽርዕ አጠራር የኤዶም አገር ናት /ማር.፫፡፰/፡፡ ኤዶም ማለትም የያዕቆብ ወንድም የዔሳው ሌላ ስሙ ነው /ዘፍ.፳፭፡፴/፡፡ ከእርሱ የተገኙ ሕዝቦችም ኤዶማውያን ይባላሉ፡፡ አገራቸውም “የኤዶም አገር፣ የሴይር ምድር” እየተባለች ትጠራለች /ዘፍ.፴፪፡፫/፡፡

ኤዶም ከጥንት አንሥቶ የወንድሙ የ ቅዱስ ያዕቆብ ጠላት ነው፡፡ የቅዱስ ያዕቆብ ልጆች (እስራኤላውያን) ከግብጽ የ፬፻፴ ዓመታት ባርነት በኋላ ወደ አገራቸው ሲመለሱ “በምድሬ አታልፍም” ብሎ የከለከላቸውም ስለዚኹ ነው /ዘኅ.፳፡፲፰/፡፡ ንጉሥ ዳዊት ኤዶማውያንን ድል አድርጓቸው ነበር፤ በአገራቸው ላይ ጭፍሮችን አስቀምጦም ግብር ያስገብራቸው ነበር /፪ኛ ሳሙ.፰፡፲፫-፲፬/፡፡ በኋላ ላይ ግን ለይሁዳ እንዳይገብር ሸፍተዋል፤ በዳዊት ልጆች ላይም በየጊዜው አደጋ ይጥሉ ነበር /፪ኛ ነገ.፰፡፳/፡፡

ኤዶማውያን በይሁዳ ላይ በሚደርሰው ማንኛውም ዓይነት ችግር ደስ ይሰኙ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ አይሁዳውያን በባቢሎናውያን በተማረኩ ጊዜ የልብ ልብ ይሰማቸው ነበር፡፡ አይሁዳውያን በባቢሎናውያን እንዲማረኩም የራሳቸው የኾነ አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡ ከመጽሐፉ ማንበብ እንደምንችለው ይሁዳ በባቢሎን ጭፍሮች ስትወረር፡- ኤዶም ከወራሪዎቹ አንዱ ነበር፤ በወንድሞቹ ይኸውም በይሁዳ ልጆች ጥፋት ደስ ይለው ነበር፤ በአይሁድ ጭንቅ ቀን በትዕቢት ይናገር ነበር፤ ሀብታቸውን ይወስድ ዘንድ እጁ ዘርግቷል፤ ከጠላት አምልጠው የሸሹትን ለመግደል በመንታ መንገድ ላይ ቆሞ ይጠብቅ ነበር፤ ከምርኮ የቀሩትን ደግሞ ከተደበቁበት እየፈለገ ለጠላት አሳልፎ ይሰጥ ነበር /ቊ.፲፩-፲፬/፡፡ #እግዚአብሔር ግን በነቢያቱ በእነ ነቢዩ ኤርምያስ፣ ሕዝቅኤል፣ አብድዩ፣ ሶፎንያስ እና በሌሎችም አድሮ ከዚኽ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ አስጠነቀቃቸው፤ በእነርሱ ላይ የሚመጣውንም ፍርድ ተናገረባቸው፡፡

#እግዚአብሔር ግን ለልጆቹ እጅግ ቀናተኛ አምላክ ነውና ኤዶም ይሁዳን በፈረደበት ፍርድ እንደሚፈርድበት ተናግሯል /ቊ.፲፭/፡፡ እንክርዳድ ዘርቶ ስንዴ ማጨድ አይቻልምና፥ ኤዶም ክፋትን እንደዘራ ፍዳው በራሱ ላይ እንደሚመለስ ተናግሯል፡፡ ይኸውም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡- “ሰው ራሱን ካልጐዳ በስተቀር ማንም ሊጐዳው አይችልም” እንዳለው ነው፡፡ ቀጥሎም #እግዚአብሔር የጽዮን ተራራ ክፉ በሚያደርጉ ኹሉ ላይ የሚያቃጥል እሳትን እንደምታወጣ ተናገረ፡፡ ይኸውም #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ነው /ቊ.፲፯-፲፰/፡፡

በአጠቃላይ መጽሐፉ አንድ ሰው በገዛ ወንድሙ ጉዳት ደስ ሊለው እንደማይገባና ይልቁንም ሊያዝንለትና ከተቻለውም ሊረዳው እንደሚገባ የሚያስረዳ ነው፡፡

መጽሐፉ የሚያልቀው፡- “… መንግሥቱም ለ #እግዚአብሔር ይኾናል” ብሎ በማወጅ ነው፡፡ ይኸውም “በያዕቆብ ቤትም ለዘለዓለም ይነግሣል፤ ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም” እንደተባለ ስለ #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የሚናገር ነው። /ሉቃ.፩፡፴፫/፡፡

#ከዚኽ_ምን_እንማራለን?

➣ኤዶም “የወንድሜ ችግር የእኔ ችግር አይደለም፤ የወንድሜ ውርደት የእኔ ውርደት አይደለም” ብለው ለሚያስቡ ኹሉ አርአያ ነው፡፡ ዛሬ የወንድማችንን ችግር እንደ ራሳችን ችግር የማንወስድ ሰዎች ካለን እኛ አዲሶቹ ኤዶሞች ኾነናል ማለት ነው፡፡

➣ኤዶም እንኳንስ ወንድሙን ያዕቆብን ሊረዳው ቀርቶ አልፎ ተርፎም ጉዳት ሲያደርስበት የነበረ “ወንድም” ነው፡፡ ዛሬም መርዳት እንኳን “ባንችል”፥ አልፈን ተርፈንም ወንድሞቻችንን የምንጐዳ ከኾነ ቃሉ እንደሚናገር ፍዳን በራሳችን ላይ የምንጨምር ኤዶማውያን ኾነናል ማለት ነው /ቊ.፲፭/፡፡

➣ኤዶም ጥልንና መለያየትን የሚሰብክ ወንድም ነው፡፡ ዛሬም ከቤተ ክርስቲያን ባሕርይ ጋር የማይስማማ መለያየትን የምንሰብክ ከኾነ ስማችን “ክርስቲያን” ሳይኾን “ኤዶማውያን” ነው፡፡

#ኤዶም ስለ ምስር ወጥ ብሎ ብኵርናውን የሸጠ ሰው ነው፡፡ ዛሬም ሰማያዊውን መና ረስተን ስለ ምድራዊ ምስር ብቻ የምንባክን ከኾነ ዜግነታችን ክርስቶሳዊ መኾኑ ቀርቶ ኤዶማዊ ኾኗል ማለት ነው፡፡ ታላቅ መኾናችን ቀርቶ ታናሽ ኾነናል ማለት ነው፡፡

➣ኤዶም ማለት መሬት ማለት ነው፡፡ ስለዚኽ ሐሳባችን ኹሉ ኤዶማዊ ከኾነ ሰማያውያን መኾናችን ቀርቶ ምድራዊያን ነን ማለት ነው፡፡ የፊተኛው ሰው የአዳም መልክ ይዘናል እንጂ የኋለኛ ሰው የ #ክርስቶስን መልክ አልያዝንም /፩ኛ ቆሮ.፲፭፡፵፯/፡፡ የሚበሰብሰው ደግሞ የማይበሰብሰውን አይወርስም፡፡

✍️ኹሉን የሚገዛ #ጌታ_አምላካችን በኹለንተናችን ላይ ነግሦ ኤዶማዊ ማንነታችንን ይሻርልን አሜን!
#ኅዳር_24

#አንድ_አምላክ_በሆነ_በአብ_በወልድ_በመንፈስ_ቅዱስ ስም
ኅዳር ሃያ አራት በዚች ቀን #የሃያ_አራቱ_ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፣ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ነው፣ #የአቡነ_ዜና_ማርቆስ ልደታቸው ነው፣ #ቅዱስ_አዝቂር_ሰማዕት ከአርባ ስምንት ሰዎች ጋር በሰማዕትነት ያረፈበት ፣ #ቅዱስ_አባ_ዮሴፍ_ዘሀገረ_ፃን ያረፈበት ዕለት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ሃያ_አራቱ_ካህናተ_ሰማይ

ኅዳር ሃያ አራት በዚህች ቀን በ #እግዚአብሔር ዙፋን ዙሪያ የሚኖሩ የሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው ።

እሊህም ሥጋ የሌላቸው ረቂቃን የእውነት ካህናት የሆኑ ከቅዱሳን ሁሉ በላይ የሆኑና ከሰማይ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍ ያሉ ናቸው እነርሱም ለ #እግዚአብሔር ቀራቢዎች በመሆን ለሰው ወገን የሚማልዱ ከእጃቸው ውስጥ ካለ ማዕጠንት ጋር እንደ ዕጣን የቅዱሳንን ጸሎት የሚያቀርቡ ናቸው ያለእነርሱም አቅራቢነት ጽድቅና ምጽዋት ወደ #እግዚአብሔር አይቀርብም።

ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ ብሎ እንደተናገረ። በዙፋኑ ዙሪያ ሃያ አራት መንበሮች አሉ በእነዚያ መንበሮች ላይም ሃያ አራት አለቆች ተቀምጠዋል ነጭ ልብስ ለብሰዋል በራሳቸውም ላይ የወርቅ አክሊል አለ።

ሁለተኛም እንዲህ አለ ሌላም መልአክ መጥቶ በመሠዊያው ፊት ቆሞ የወርቅ ጽንሐሕ ይዟል በመንበሩ ፊት ባለ በወርቁ መሠዊያ ላይም የቅዱሳንን ሁሉ ጸሎት ያሳርግ ዘንድ ብዙ ዕጣንን ሰጡት ። የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳኑ ጸሎት ጋር በዚያ መልአክ እጅ ወደ #እግዚአብሔር ፊት ዐረገ ።

የነበረ የሚኖር የአማልክት አምላክ #እግዚአብሔር_ቅዱስ_ቅዱስ_ቅዱስ ነው እያሉ በመዓልትና በሌሊት ዕረፍት የላቸውም ። እሊህም እንስሶቹ ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆን በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለሱ እንዲህ እያሉ ክብር ምስጋና አቀረቡ ።

እሊህ ሃያ አራቱ አለቆች አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አውርደው ለዘላለሙ ሕያው ለሚሆኑ በዙፋን ላይ ለተቀመጠ ለእሱ ሰገዱለት ። አክሊላቸውንም ወደ ዙፋኑ ፊት ወስደው አቤቱ ፈጣሪያችን ኃይልና ምስጋና ክብር ላንተ ይገባል ይሉታል አንተ ሁሉን ፈጥረሃል የተፈጠረውም ሁሉ በአንተ ፈቃድ ይኖራልና ።

እነርሱ በ #እግዚአብሔር ዘንድ በባለሟልነት እጅግ የቀረቡ መሆናቸውንና ስለሁላችን የአዳም ልጆች ስለሚለምኑና ስለሚማልዱ ከብሉይና ከሐዲስ የከበሩ መጻሕፍት ምስክር ሁነዋል ስለዚህም የበዓላቸውን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሱራፌል(ካህናተ ሰማይ) ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት

በዚህች ቀን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የ #ሥሉስ_ቅዱስን መንበር እንዳጠኑ፡- አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦላቸው ነው በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ የነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም መልአኩን ተከትለው ሐይቁን በእግራቸው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኩሰዋቸዋል፡፡

ከዚህም በኋላ አባታችን በዚያው በሐይቅ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ አክፍሎትንም በየሳምንቱ ያከፍላሉ፣ ከእሁድና ከቅዳሜ በቀር ምንም አይቀምሱም ነበር፡፡ በእነዚህም ዕለት የአጃ ቂጣ ወይም የዱር ቅጠል ይመገቡ ነበር፡፡ ወዛቸው እንደ ውኃ ፈስሶ ምድሪቷን እስኪያርሳት ድረስ እስከ 70 ሺህ ስግደትንም በመስገድ ራሳቸውን እጅግ አደከሙ፡፡ በእነደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ ላይ ሳሉ ነው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ድንገት ነጥቆ ወስዶ ከ #ሥሉስ_ቅዱስ ዙፋን ፊት ያቆማቸው፡፡

ከዚህ በኋላ ስለሆነው ነገር ራሳቸው አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሲናገሩ ‹‹…ከዚህ በኋላ መልአኩ ወደ ሰማይ አውጥቶ ከመጋረጃው ውስጥ አስገብቶ ከ #ሥላሴ ዙፋን ፊት አቆመኝና ሰገድኩለት፡፡ ከዚያ አስቀድሞ በማላውቀው በሌላ ምስጋና አመሰገንኩት፡፡ ‹ተክለ ሃይማኖት ክፍልህ ከ24ቱ ካህናቶቼ ጋር ይሁን› የሚል ቃል ከዙፋኑ ውስጥ ወጣ፡፡ የወርቅ ጽና አምጥተው ሰጡኝና ከእነርሱ ጋር በአንድነት አጠንሁ፡፡ ምስጋናዬ ከምስጋናቸው ጋር ልብሴም እንደልብሳቸው ሆነ፡፡ ፈጣሪዬንም በሦስትነቱ ተገልጦ አየሁት፡፡ በጸሎትህ የሚታመን ሰው ሁሉ ስለአንተ ይድናል አለኝ…..›› (ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገጽ 216-223)

ይህንን ታላቅ በዓል ነው ዛሬ የምናከብረው፡፡ አቡነ ተክለሃይማኖት እንኳን አንደበታቸው የለበሱትም ልብሳቸውም ጭምር #እግዚአብሔርን በሰው አንደበት እንደሚያመሰግን በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፏል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ አቡነ ተክለ ሐይማኖት ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አቡነ_ዜና_ማርቆስ

በዚህች ቀን አቡነ ዜና ማርቆስ በወንጌላዊ በቅዱስ ማርቆስ ብስራት እንደተወለዱ፦ አባታችን ዜና ማርቆስ ሀገራቸው ጽላልሽ አውራጃ ምድረ ዞረሬ ስትሆን ትውልዳቸው ከነገደ ሌዊና ከእስራኤል ነገሥት ወገን ነው፡፡ ወላጆቻቸው ልጅ በማጣት ሲያዝኑ አንድ ዕለት ሐዋርያውና ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ወደ እናታቸው ማርያም ዘመዳ ሌሊት መጥቶ ገድሉና ትሩፋቱ በዓለም ሁሉ የመላ ጻድቅ ልጅ እንደምትወልድ አበሰራት፡፡

ለአባቱ ለቀሲስ ዮሐንስም እንዲሁ ተገልጦለት ‹‹ሚስትህ ማርያም ዘመዳ የካቲት 24 ፀንሳ ኅዳር 24 ቀን ይኸውም በካህናተ ሰማይ በዓል ቀን ትወልዳለች፣ ስሙም ዜና ማርቆስ ይባላል›› በማለት ብስራቱን ነግሮታል፡፡

በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ብሥራት መሠረት አባታችን ዜና ማርቆስ በዚህች ዕለት ኅዳር 24 ቀን በተወለዱ ጊዜ ቅዱስ ዑራኤልና ቅዱስ ሩፋኤል የብርሃን ልብስ አልብሰው በክንፋቸው ሲጋርዱአቸው ለሰዎች ሁሉ ታይቷል፡፡ የአቡነ ሳሙኤል ዘወገግ አባት ቅዱስ እንድርያስና የአቡነ ተክለሃይማኖት አባት ቅዱስ ጸጋ ዘአብ እስኪደነቁ ድረስ ይህን በዓይናቸው ተመልክተዋል፡፡ ሁለቱ መላእክትም አቡነ ዜና ማርቆስን ከእናታቸው ዕቅፍ ወስደው ወደ ሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ መቃብር ወስደው ለቅዱስ ማርቆስና ለቅዱሳን ጳጳሳት አስባርከዋቸው መልሰው ለእናታቸው ሰጧቸው፣ እናታቸው ግን ይህን አታውቅም ነበር፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን በእግራቸው ቆመው ‹‹አንድ አምላክ ለሆኑ ለ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ እሰግዳለሁ›› ብለው ሦስት ጊዜ አምላካቸውን አመስግነው ሰግደዋል፡፡

በ40 ቀናቸውም ሲጠመቁ የሚያጠምቃቸው ካህን የአባታቸው ወንድም እንድርያስ ውኃው ሲፈላ አይቶ ሸሽቷል፡፡ መልአኩም እንዳይፈራ ነግሮት ለእርሱም ተአምር እንደሚደረግለት አስረዳው፡፡ ቅዱስ እንድርያስም ዕድሜው 72 ነበርና ራሰ በራ ስለነበር አባታችንን ባጠመቀበት በውኃው ራሱን ቢታጠብበት ጸጉር አብቅሏል፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ይህን አይቶ አደነቀ፡፡ ያችም ውኃ ሌሎች በጣም ብዙ ተአምራትን አደረገች፡፡
አቡነ ዜና ማርቆስ አንድ ዓመት በሆናቸውም ጊዜ ቤተክርስቲያን ውስጥ እየዳኹ ሲሄዱ መልአክ በክንፎቹ አቅፎ ነጥቆ ወደሰማይ ወስዶ #ጌታችንና #እመቤታችን ጋር አቅርቦ አስባርኳቸዋል፡፡ እንዲሁም የ15ቱን ነቢያት፣ የ12ቱን ሐዋርያት የ72ቱን አርድእት፣ ሃይማኖታቸው የቀና የ318ቱን ሊቃውንት፣ የጻድቃንን፣ የሰማዕታትን የእነዚህን ሁሉ በረከት እንዲቀበሉ ካደረጋቸው በኋላ ወደዚያች ቤተክርስቲያን መለሳቸው፡፡ የአቡነ ዜና ማርቆስን የዕረፍታቸውን በዓል ከ9 ቀናት በኋላ ታኅሣሥ 3 ቀን ስለምናከበር አምላካቸው ከዕረፍታቸው ቀን ያድርሰንና ያንጊዜ ሙሉን ዜና ገድላቸውን እናየዋለን፡፡ በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አዝቂር_ሰማዕት

በዚችም ዕለት የናግራን አገር ቄስ የከበረ አዝቂር የሐሚር ንጉሥ ሰራብሄል በነገሠበት ወራት ከእርሱ ጋር ካሉ አርባ ስምንት ሰዎች ጋር በሰማዕትነት አረፈ ።

ይህም ንጉሥ አዝቂርን ወደ ወህኒ አስገብተው እንዲዘጉበት ጠባቂዎቹንም ከሰው ወገን ማንም እንዳይገባ ብሎ አዘዘ ። ቅዱስ አዝቂርም በጸለየ ጊዜ የወህኒ ቤቱ ደጃፍ ተከፈተና ሃምሳ ሰዎች ወደርሱ ገቡ እርሱም በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ።

ንጉሥ ሰራብሄልም በሰማ ጊዜ ከወህኒ ቤት አውጥተው ወደሌላ አገር እንዲወስዱት አዘዘ በጉዞም ላይ ስሙ ኪርያቅ ከሚባል ሰው ጋር ተገናኘ ቀሲስ አዝቂርም ኪርያቅን ኪርያቅ ሆይ ላንተ የምሥራች ይገባል ለሰማዕትነት ይወስድሃልና አለው ። የንጉሥ ሎሌዎችም ሰምተው አሥረው ከእርሱ ጋር ወሰዱት ። ዳግመኛም ሁለት ሰዎች ተገናኙትና ስለ #ክርስቶስ አጥምቀን አሉት ያን ጊዜም ቅዱስ አዝቂር ጸለየና ከበረሀ ቦታ ውኃ አፍልቆ ከኪርያቅ ጋር አጠመቃቸው ።

ከዚህም በኋላ ወደበረሀ ውስጥ በደረሱ ጊዜ ለእሳቸውም ለእንስሶቻቸውም የሚጠጡት ውኃ አጥተው ወደ #እግዚአብሔር እንዲለምንላቸው ቅዱስ አዝቂርን ለመኑት በጸለየም ጊዜ ደመና መጣ በመሐል እጅ በሚታፈን መጠን በገበታ ላይ ዘነበ ሰባት መቶ ያህል ሰዎች ከእንስሶቻቸው ጋር ጠጥተው ረኩ ።

ወደ ንጉሡም በአቀረቡት ጊዜ ወደ አገራችን ያመጣኸው ይህ አዲስ ትምህርት ምንድነው አለው ቅዱስ አዝቂርም ነቢያት በኦሪት ከሰበኩት በቀር ሌላ አዲስ ትምህርት አላመጣሁም አለ ንጉሡም ይህን ሰምቶ በክርስቲያን ሃይማኖት ላይ ተዘባበተ።

ከአይሁድ መምህራንም አንዱ ተነሥቶ እንዲህ አለ ጌታዬ ሆይ ወደ አገሩ እንዲወስዱትና በዕንጨት ላይ ሰቅለው በሕይወት ሳለ በእሳት እንዲአቃጥሉት እዘዝ አለው ንጉሡም እንደ አይሁዳዊው ቃል አዘዘ።

ወደ ናግራን አገርም በአደረሱት ጊዜ በዕንጨት ላይ ሰቅለው ከበታቹ እሳትን አነደዱ ቅዱስ አዝቂርም ወደ #ጌታችን ጸለየ በዚያንም ጊዜ ከማሠሪያው ተፈትቶ ከእሳት ውስጥ በደኅና ወጣ አይሁድም በደንጊያ እንውገረው ተባብለው በወገሩት ጊዜ ደንጊያዎች ተመልሰው ከአይሁድ የሚበዙትን ገደሉ ።

ከተረፉትም ሰይፍን አንሥተው የቅዱስ አዝቂርን ራስ ቆረጡ ምስክርነቱንም ፈጽሞ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጀ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አዝቂርና በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዮሴፍ_ዘሀገረ_ፃን

በዚችም ቀን ፃን ከምትባል አገር የሆነ አባ ዮሴፍ አረፈ። ለዚህም ቅዱስ ወላጆቹ በሃይማኖት የበለጸጉ ናቸው ነገር ግን ያለርሱ ልጅ አልነበራቸውም የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት መጻሕፍት ማንበብንም እያስተማሩ መልካም አስተዳደግን አሳደጉት መልኩም እንደ ቅዱስ ያዕቆብ ልጅ ቅዱስ ዮሴፍ ያማረ ነበር በአደገም ጊዜ ሞትን የዚህንም ዓለም ኃለፊነት ማሰብ በልቡ አደረ።

ወደ አንድ ገዳምም ሒዶ መንኵሶ በጾም በጸሎት በመስገድ በተጋድሎ የተተከለ ሆኖ ጸና በአቱንም ዘግቶ በእለተ እሑድ ከቁርባን ጊዜ በቀር አይወጣም ነበር ። ዜናውም በተሰማ ጊዜ ከእርሱ በረከቱን ይቀበሉ ዘንድ በአገር ዙሪያ ያሉ ሰዎች የሚመጡ ሆኑ አባቱና እናቱም የልጃቸውን ወሬ በአጡ ጊዜ እርሱን ያገናኛቸው ዘንድ ወደ #እግዚአብሔር እየለመኑ ነበር።

ወሬውንም በሰሙ ጊዜ ስለ ልጃቸው መገኘት እንዲጸልይላቸው ወደርሱ ሔዱ እርሱ ልጃቸው እንደሆነ አላወቁምና ሰውም ገለል ባለ ጊዜ ልጃቸው መሆኑን እራሱን ገለጠላቸውና ለማንም እንዳይናገሩ አዘዛቸው ።

#እግዚአብሔርም ድንቆች ተአምራትን የማድረግ ሀብትን ሰጠው ሰይጣን እስከ ቀናበት ድረስ ወደ አገረ ገዢውም ሔዶ ይህ መነኵሴ ዮሴፍ ብዙ ገንዘብ እንዳለው አስመስሎ ነገር ስራበት ። መኰንኑም በሰንሰለት ማሰሪያዎች አሰረው። በማግሥቱም ማሰሪያዎቹ ከላዩ ወደ ምድር ወድቀው ተገኙ መኰንኑም አይቶ ደነገጠ ለቅድስናውም ተገዥ ሆነ ።

ብዙ ከተጋደለና #እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ በሰላም አረፈ። በክብርም ቀበሩት ከመቃብሩም ቁጥር የሌላቸው ብዙ ተአምራት ተገለጡ።

#,ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_ኅዳር_24 እና #ከገድላት_አንደበት)
#የኅዳር_24_ግጻዌ

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ኅዳር_24_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጢሞቴዎስ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁷ በመልካም የሚያስተዳድሩ ሽማግሌዎች፥ ይልቁንም በመስበክና በማስተማር የሚደክሙት፥ እጥፍ ክብር ይገባቸዋል።
¹⁸ መጽሐፍ፦ የሚያበራየውን በሬ አፉን አትሰር፥ ደግሞ፦ ለሠራተኛ ደመወዙ ይገባዋል ይላልና።
¹⁹ ከሁለት ወይም ከሦስት ምስክር በቀር በሽማግሌ ላይ ክስ አትቀበል።
²⁰ ሌሎቹ ደግሞ እንዲፈሩ፥ ኃጢአት የሚሰሩትን በሁሉ ፊት ገሥጻቸው።
²¹ አንድን እንኳ በአድልዎ ሳታደርግ፥ እነዚህን ያለ መዘንበል እንድትጠብቅ በእግዚአብሔርና በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በተመረጡትም መላእክት ፊት እመክርሃለሁ።
²² በማንም ላይ ፈጥነህ እጆችህን አትጫን፥ በሌሎችም ኃጢአት አትተባበር፤ ራስህን በንጽህና ጠብቅ።
²³ ስለ ሆድህና ስለ በሽታህ ብዛት ጥቂት የወይን ጠጅ ጠጣ እንጂ፥ ወደ ፊት ውኃ ብቻ አትጠጣ።
²⁴ የአንዳንዶች ሰዎች ኃጢአት የተገለጠ ነው ፍርድንም ያመለክታል፥ ሌሎችን ግን ይከተላቸዋል፤
²⁵ እንዲሁ መልካም ሥራ ደግሞ የተገለጠ ነው፥ ያልተገለጠም ከሆነ ሊሰወር አይችልም።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ያዕቆብ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹² ከሁሉም በፊት፥ ወንድሞቼ ሆይ፥ በሰማይ ቢሆን በምድርም ቢሆን በሌላ መሐላም ቢሆን በምንም አትማሉ፤ ነገር ግን ከፍርድ በታች እንዳትወድቁ ነገራችሁ አዎን ቢሆን አዎን ይሁን፥ አይደለምም ቢሆን አይደለም ይሁን።
¹³ ከእናንተ መከራን የሚቀበል ማንም ቢኖር እርሱ ይጸልይ፤ ደስ የሚለውም ማንም ቢኖር እርሱ ይዘምር።
¹⁴ ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽምግሌዎች ወደ እርሱ ይጥራ፤ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት።
¹⁵ የእምነትም ጸሎት ድውዩን ያድናል ጌታም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደ ሆነ ይሰረይለታል።
¹⁶ እርስ በርሳችሁ በኃጢአታችሁ ተናዘዙ። ትፈወሱም ዘንድ እያንዳንዱ ስለ ሌላው ይጸልይ፤ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች።
¹⁷ ኤልያስ እንደ እኛ የሆነ ሰው ነበረ፥ ዝናብም እንዳይዘንብ አጥብቆ ጸለየ፥ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር አልዘነበም፤ ሁለተኛም ጸለየ፥
¹⁸ ሰማዩም ዝናብን ሰጠ ምድሪቱም ፍሬዋን አበቀለች።
¹⁹ ወንድሞቼ ሆይ፥ ከእናንተ ማንም ከእውነት ቢስት አንዱም ቢመልሰው፥
²⁰ ኃጢአተኛን ከተሳሳተበት መንገድ የሚመልሰው ነፍሱን ከሞት እንዲያድን፥ የኃጢአትንም ብዛት እንዲሸፍን ይወቅ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 22
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁸ እርሱም፦ ፍጠን ከኢየሩሳሌምም ቶሎ ውጣ፥ ስለ እኔ የምትመሰክረውን አይቀበሉህምና ሲለኝ አየሁት።
¹⁹ እኔም፦ ጌታ ሆይ፥ በአንተ የሚያምኑትን በምኵራብ ሁሉ እኔ በወኅኒ አገባና እደበድብ እንደ ነበርሁ እነርሱ ያውቃሉ፤
²⁰ የሰማዕትህንም የእስጢፋኖስን ደም ባፈሰሱ ጊዜ፥ ራሴ ደግሞ በአጠገባቸው ስቆም ተስማምቼ የገዳዮችን ልብስ እጠብቅ ነበር አልሁ።
²¹ እርሱም፦ ሂድ፥ እኔ ወደ አሕዛብ ከዚህ ወደ ሩቅ እልክሃለሁና አለኝ። ወይም👇

ሐዋርያት 12
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶ ሄሮድስም ሊያወጣው ባሰበ ጊዜ፥ በዚያች ሌሊት ጴጥሮስ በሁለት ሰንሰለት ታስሮ ከሁለት ወታደሮች መካከል ተኝቶ ነበር፤ ጠባቂዎችም በደጁ ፊት ሆነው ወኅኒውን ይጠብቁ ነበር።
⁷ እነሆም፥ የጌታ መልአክ ቀረበ በቤትም ውስጥ ብርሃን በራ፤ ጴጥሮስንም ጎድኑን መትቶ አነቃውና፦ ፈጥነህ ተነሣ አለው። ሰንሰለቶቹም ከእጁ ወደቁ።
⁸ መልአኩም፦ ታጠቅና ጫማህን አግባ አለው፥ እንዲሁም አደረገ።
⁹ ልብስህንም ልበስና ተከተለኝ አለው። ወጥቶም ተከተለው፤ ራእይንም የሚያይ ይመስለው ነበር እንጂ በመልአኩ የሚደረገው ነገር እውነት እንደ ሆነ አላወቀም።
¹⁰ የመጀመሪያውንና የሁለተኛውንም ዘብ አልፈው ወደ ከተማ ወደሚያወጣው ወደ ብረቱ መዝጊያ ደረሱ፤ እርሱም አውቆ ተከፈተላቸው፤ ወጥተውም አንዲት ስላች አለፉ ወዲያውም መልአኩ ከእርሱ ተለየ።
¹¹ ጴጥሮስም ወደ ልቡ ተመልሶ፦ ጌታ መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና የአይሁድ ሕዝብ ይጠብቁት ከነበረው ሁሉ እንደ አዳነኝ አሁን በእውነት አወቅሁ አለ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኅዳር_24_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ባርክዎ ለ #እግዚአብሔር ኵልክሙ መላእክቲሁ። ጽኑዓን ወኃያላን እለ ትገብሩ ቃሎ። ወእለ ትሰምዑ ቃለ ነገሩ"። መዝ 102፥20።

#ትርጉም፦ “ቃሉን የምትፈጽሙ፥ ብርቱዎችና ኃያላን፥ የቃሉንም ድምፅ የምትሰሙ መላእክቱ ሁሉ፥ #እግዚአብሔርን ባርኩ።” መዝ 102፥20።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ኅዳር_24_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 13
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³⁶ በዚያን ጊዜ ሕዝቡን ትቶ ወደ ቤት ገባ። ደቀ መዛሙርቱም ወደ እርሱ ቀርበው፦ የእርሻውን እንክርዳድ ምሳሌ ተርጕምልን አሉት።
³⁷ እርሱም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ መልካምን ዘር የዘራው የሰው ልጅ ነው፤ እርሻውም ዓለም ነው፤
³⁸ መልካሙም ዘር የመንግሥት ልጆች ናቸው፤
³⁹ እንክርዳዱም የክፉው ልጆች ናቸው፥ የዘራውም ጠላት ዲያብሎስ ነው፤ መከሩም የዓለም መጨረሻ ነው፥ አጫጆችም መላእክት ናቸው።
⁴⁰ እንግዲህ እንክርዳድ ተለቅሞ በእሳት እንደሚቃጠል፥ በዓለም መጨረሻ እንዲሁ ይሆናል።
⁴¹ የሰው ልጅ መላእክቱን ይልካል፥ ከመንግሥቱም እንቅፋትን ሁሉ ዓመፃንም የሚያደርጉትን ይለቅማሉ፥
⁴² ወደ እቶነ እሳትም ይጥሉአቸዋል፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።
⁴³ በዚያን ጊዜ ጻድቃን በአባታቸው መንግሥት እንደ ፀሐይ ይበራሉ። የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ሠለስቱ_ምዕት ወይም የ #ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘሥሩግ_ቅዳሴ ነው። መልካም የሃያ አራቱ #ካህናተ_ሰማይ፣ የ #አቡነ_ተክለሃይማኖት በዓል፤ የ #አቡነ_ዜና_ማርቆስ የልደት በዓልና የጾም ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2025/12/02 12:14:23
Back to Top
HTML Embed Code: